Wednesday 17 July 2013

ልፋ ያለው በሕልሙ ክብደት ይሸከማል!



ካህን ኃጢአት ያስተሰርያል?

እንደኛው ኃጢአት የሚሰራ ሰው እንዴት ኃጢአትን የመሰረዝ ሥልጣን አለው? ካህኑ ማን ነውና ከእኔ ይበልጣል? እውነት ግን እንደኛው ኃጢአተኛ ሰው እንዴት ኃጢአትን ያስተሰርያል???

ይህን የሚጠይቁ ብዙ ናቸው። "ልፋ ያለው በሕልሙ ክብደት ይሸከማል" ያልኳችሁም ለዚሁ ነው። ጴጥሮስ ጌታን አላቅም ብሏልና እንዴት የሐዋርያቱ አለቃ ሆነ? እያለ የሚጠይቅ ልፋ ያለው ሰው ነው። እናንተዬዋ ሐዋርያቱ ግን ጴጥሮስን እንዴት ዝም አሉት? አንተ ኃጢአትን ሰርተሃልና አለቃችን አትሆንም ብለው መፈንቅለ ሐዋርያዊ ሥልጣን ለምን አላደረጉም?

ሰዎች ሆይ ካህኑ ራሱ ንስኃ እንደሚገባ አታውቁምን? ካህኑም ጳጳሱም ፓትርያርኩም ኃጢአታቸውን ልክ እንደኛው እንደሚናዘዙ አታውቁምን?

እስኪ ደግመን እንጠይቅ ፦ ካህን ኃጢአት ያስተሰርያል? ለጥያቄው መፅሐፍትን አብረን እንመርምርና መልሱን ለሕሊናችሁ አሳልፌ እሰጣለሁ።

ምስጢረ ቀንዲል፦ ምስጢረ ቀንዲል በካህኑ ጸሎት እና ቡራኬ በሽተኛው ሰውዪ በተባረከው ዘይት በመቀባቱ ከበሽታው መዳንን ከኃጥያት መንፃትን የሚያስገኝ ምሥጢር ነው። ይኸውም ምሥጢር ለአካለ ስጋም ለአካለ ነፍስም ጤንነትን ለመስጠት የእግዚአብሔር ጸጋንም ለማስተላለፍ የሚችል ነው። ቀንዲል ማለት መብራት ማለት ነው። ምስጢረ ቀንዲል በሚደረግበት ጊዜ መብራት ይበራል ስለዚህም ስያሜው ከስርዓቱ አፈጻጸም ተዋስዷል (ዘፍ 40፡4 ዘኁሉ 4፡9)።

ይህንን ምሥጢር የመሰረተው ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። አስራሁለቱን ሐዋርያት ጠርቶ ስልጣንን በሰጣቸው ጊዜ የመፈወስ ስልጣን ሰጥቷቸዋል (ማቴ 10፡1 ማር 6፡7 ሉቃ 9፡1)። “በወጡ ጊዜም አስተምሮ ንስሀ ይገቡ ዘንድ እጅግም ሰይጣናትን አውጡ በዘይትም ብዙ ድውያንን ቀቡ አድኗቸውም” (ማር 6፡12-13)። ከትንሳኤ በኋላ ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድውይ የመፈውስ ሃይል ሰጥቷቸዋል። (ማቴ 6፡17-18) ሐዋርያትም ምስጢር መጋቢዎች እንደመሆናቸው በትዕዛዙ መሰረት ሲሰሩበት ኖረዋል (1ኛ ቆሮ 4፡1)። ቀጥሎ ቀሳውስቱን በዘይት እየቀቡና እየፀለዩ ህሙማንን እንዲፈውሱ ሐዋርያት አዘዋል። “ከእናንተ የታመመ ማንም ቢኖር የቤተክርስቲያን ቀሳውስትን ወደ እርሱ ይጥራ በጌታም ስም እርሱን ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት /ምስጢረ ቀንዲል/ የእምነት ጸሎት ድውይን ያድናል፣ ጌታም ያስነሳዋል ((ኃጥያትም ሰርቶ እንደሆን ይሰረይለታል)) /ምስጢረ ንስኃ/ ያዕ 5፡14-15 ቤተክርስቲያን ይህን ቅዱስ ምስጢር ሲወርድ ሲዋረድ በመጣው ትውፊት መሰረት ስትፈጽመው ትኖራለች በመፈጸምም ላይ ትገኛለች።

ምስጢረ ቀንዲል የሚፈጸመው ከንጹህ የወይራ ዘይት ነው። ቅብዐ ቅዱስ እየተባለ ይጠራል። ማንም ሰው በማንኛውም ጊዜ ሲታመም ካህኑን ጠርቶ ምስጢረ ቀንዲል ሊጠይቅና ሊፈጸምለት ይችላል። ቅባ ቅዱሱን ጳጳስ ይባርካል። ምስጢረ ቀንዲል በቤተክርስቲያን፣ በመኖሪያ ቤት እና በሆስፒታል ሊፈጸም ይችላል። በሽተኛው ከመቀባቱ በፊት ኃጢያቱን ይናዘዛል ከዚያም ዘይቱ ቀርቦ ሥርአተ ጸሎቱ ይፈጸማል። በመቀጠል ካህኑ በሽተኛውን በጭንቅላቱ ላይ እጁን ጭኖ ይጸልያል በመጨረሻም አምስቱን ህዋሳት ማለት አይኑን፣ አፉን፣ ጆሮውን፣ አፍንጫውን እና እጁን ይቀባል። በዐይኑ አይቶ፣ በአንፍጫው አሽትቶ፣ በጆሮው ሰምቶ፣ በአፉ ተጋግሮ፣ በእጁ ዳሶ ለሰራው ኃጢያት ስርየት እንዲሆንለት ሲል ነው። በዚህ ጊዜ በሽተኛው በሥጋ ደዌ ደክሞ የነበረው መንፈሳዊ በሽተኛው ሥርየት ያገኛል። በዚህ በሚታየው ምሥጢር የማይታይ ፀጋ ይገኝበታል።

የዮሐንስ ወንጌል 20
23 ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል አላቸው።

ይህ የተነገረው ለማን ይሆን? ይህች ሥልጣን የማን ትሆን? አንዱ ተነስቶ ኃጢአትህን ያዝኩብህ ቢል ማን ይሰማዋል? ይህን የማድረግ ሥልጣን አለው? እንግዲያውስ ይህች ታላቅ ሰማያዊ ሥልጣን ከቶ የማን ናት???

የማርቆስ ወንጌል 1
4 ዮሐንስ በምድረ በዳ እያጠመቀ የንስሐንም ጥምቀት ለኃጢአት ስርየት እየሰበከ መጣ።
5 የይሁዳም አገር ሁሉ የኢየሩሳሌምም ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ ይወጡ ነበር፥ ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር።
(ኃጥያትም ሰርቶ እንደሆን ይሰረይለታል)) (ያዕ 5፡14-15)

ፕሮቴስታንት ዘመዶቻችን ሆይ ካህን ኃጢአት ያስተሰርያል?

Tuesday 16 July 2013

ፍቅር ማን ነው?



ሆድ ሲሞላ ፍቅሩ ሌላ ፤ ሆድ ሲጎድል ሰው ያጋድል አሉ!

እስኪ አንድ ታሪክ ላውጋችሁ፦ አንድ የዋህ አባት ነበር አሉ። ይህን የዋህነቱን ያዩ አሥራ ሦስት ሽፍቶች ጩቤ ጎራዴ ሳንጃ በልብሳቸው ውስጥ ደብቀው የዚህን ሰው ቤት አንኳኩ። ይህ ሰው የዘመኑ አብርሐም ይባላልና እንግዶቹን በደስታ ተቀበለ። ሲቆጥራቸው 13 ሆኑ። ጌታ ከአስራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋ ቤቴ መጣ ብሎ እጅግ ደስ ደስ አለው። ጌታ የቱ ይሆን ? እያለ ጠየቃቸው። ጴጥሮስ የቱ ነው? ዮሐንስና ያዕቆብስ ? እያለ ጠየቃቸው። እግራቸውን አጥቦ ምግብ አቅርቦ በታላቅ ፍቅር ተቀበላቸው። ሽፍቶቹ ይህን ሁሉ ደግነቱን አዩና ልባቸው ራራ። ሊገድሉት መጥተው በፍቅሩ ተሸንፈው ከእግሩ ስር ተንበረከኩ። ኃያላን ጉልበተኛ ቢሆኑም በፍቅር ተሸነፉ። በሽፍታነት የዋኙበት ይህችን ዓለም ንቀው የቅድስና ሕይወት መኖር ጀመሩ!

ፍቅር ማን ነው?

ፍቅር ኃያል ነው ጉልበተኛውን ያንበረክካልና
ፍቅር ጉልበተኛ ነው ትዕቢተኛውን ትሁት ያደርጋልና
ፍቅር ጠቢብ ነው በጥላቻ የታወረውን ዓይኑን ያበራልና
ፍቅር ታጋሽ ነው ዕልኸኛውን ያረጋጋልና
ፍቅር ይቅር ባይ ነው የበደለን ያጸጽታልና
ፍቅር ጥበበኛ ነው ተሳዳቢውን ይመክራልና
ፍቅር መካሪ ነው ስሜታዊውን ይገስጻልና
ፍቅር ሩህሩህ ነው የካደውን ዳግም ይወዳልና
ፍቅር ጤና ነው የሕሊና ሰላም ይሰጣልና
ፍቅር ቸር ነው የነፈገን አይነፍግምና
ፍቅር ርግብ ነው ቂም አይዝምና
ፍቅር ብሩህ ፊት ነው አይመቀኝምና
ፍቅር የተረጋጋ ነው በቶሎ አይቆጣምና
ፍቅር የዋህ ነው በደልን አይቆጥርምና

ፍቅር ማን ነው?

ፍቅርማ እንደ ረጅም ፈትል ከዙፋኑ የወረደው ነው
ዝቅ ዝቅ ብሎ የፈጠረውን እግር ያጠበው ነው
እንደሚታረድ በግ አንገቱን ለሸላቾቹ የሰጠው ነው

ፍቅርማ በመስቀል ላይ እጁን የዘረጋው ነው

የፍቅር አምላክ ሆይ ፍቅርህን አልብሰን፤ አሜን።

http://yonas-zekarias.blogspot.com/

Monday 15 July 2013

//የፕሮቴስታንት መዝሙሮችን እንፈትሽ//



ሁለት አይወዱ ከመነኮሱ አይወልዱ አሉ!

መንፈሳዊነትን ከዓለማዊነት ማን አንድ አደረገው? ዓለማዊያን በሄዱበት ጎዳና መንፈሳዊያን እንዴት ይሄዳሉ? 

መዝሙረ ዳዊት 137
1 በባቢሎን ወንዞች አጠገብ በዚያ ተቀመጥን ጽዮንንም ባሰብናት ጊዜ አለቀስን።
2 በአኻያ ዛፎችዋ ላይ መሰንቆቻችንን ሰቀልን።
3 የማረኩን በዚያ የዝማሬን ቃል ፈለጉብን፥ የወሰዱንም። የጽዮንን ዝማሬ ዘምሩልን አሉን።
4 ((የእግዚአብሔርን ዝማሬ በባዕድ ምድር እንዴት እንዘምራለን?))
5 ኢየሩሳሌም ሆይ፥ ብረሳሽ፥ ቀኜ ትርሳኝ።
6 ባላስብሽ፥ ምላሴ በጕሮሮዬ ይጣበቅ

በዳዊት መዝሙር እንዳየነው የእግዚአብሔርን ዝማሬ እንኳን እንደፈለግነው ልንዘምር ቀርቶ በባዕድ ሀገር እንኳን አንዘምርም የተባለበት ዘመን ነበር። አሁን አሁን ግን መዝሙርና ዘፈን መንታ እህትማማች ሆነዋል። ዘፈን ላይ ያየነውን ዝላይ አንዳች ሳይለወጥ በመዝሙር እናየዋለን። ሁሉ በሥርዓት ይሁን የሚለው ቃል መዝሙሩ ላይ የሚሰራ አይመስለኝም። የተረጋጋ መዝሙር ሰምቼም አላውቅም። ዓለማዊው ዘፈን እንኳን አንዳንዴ ረጋ ይላል። መንፈሳዊያን እንዴት መርጋት አቃታቸው? መንፈሳዊነትን ከዓለማዊነት ማን አንድ አደረገው? ዓለማዊያን በሄዱበት ጎዳና መንፈሳዊያን እንዴት ይሄዳሉ? ((የእግዚአብሔርን ዝማሬ በባዕድ ምድር እንዴት እንዘምራለን?)) የእግዚአብሔር ምስጋና በተቀደሰች ቦታ ትዘመራለች እንጂ እንዴት በየአዳራሹ ይዘመራል? አዳራሽ ለስብሰባ ለዕድር ለዘፈንም ይኬዳል። አለማዊያን በዘፈኑበት አዳራሽ የእግዚአብሔርን ዝማሬ መዘመር ከቶ አይገባም።

ፕሮቴስታንት ዘመዶቻችን ሆይ ዳዊት እንዴት እያነባ እንደዘመረ የንስኃ መዝሙሩን ስሙ፦
መዝሙረ ዳዊት 6
1 አቤቱ፥ በቍጣህ አትቅሠፈኝ፥ በመዓትህም አትገሥጸኝ።
2 ((ድውይ ነኝና አቤቱ፥ ማረኝ)) አጥንቶቼ ታውከዋልና ፈውሰኝ።
3 ነፍሴም እጅግ ታወከች አንተም አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ነው?
4 አቤቱ፥ ተመለስ ነፍሴንም አድናት፥ ስለ ቸርነትህም አድነኝ።
5 በሞት የሚያስብህ የለምና፥ በሲኦልም የሚያመሰግንህ ማን ነው?
6 በጭንቀቴ ደክሜያለሁ ((ሌሊቱን ሁሉ አልጋዬን አጥባለሁ፥ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ))
7 ((ዓይኔ ከቍጡ ዕንባ የተነሣ ታወከች ከጠላቶቼ ሁሉ የተነሣ አረጀሁ))

እንግዲህ ምን እንላለን፤ ዘመዶቻችን ሆይ የዳዊት ዕንባ በጉንጫችሁ ላይ ወርዶ ያውቃል? ብዙዎቻችሁ እንደ ዳዊት ልብሳችን እየወለቀ እንዘምራለን ትላላችሁ፤ ታድያ እንደ ዳዊት እያለቀሳችሁ ዘምራችሁ ታውቃላችሁ? መልሳችሁ ለጊዜው ይለፈን። ቅ/ጴጥሮስም እንደ ጅረት ወንዝ ስለንስኃው አነባ። ፕሮቴስታንት ዘመዶቻችን ሆይ ስለ ኃጢአታችሁ መቼ ይሆን የምታነቡት? እንደ ማርያም እንተ ህፍረት እግሩ ላይ ዝቅ ብላችሁ ሽቱ ቀብታችሁ ማረኝ የምትሉት መቼ ነው? እንደ በጥለሚዮስ የዳዊት ልጅ ሆይ ማረኝ የምትሉትስ መቼ ይሆን?
ይህን ማለታችን ቤተክርስቲያን ሙሾ የሚወርድባት ለቅሶ ቤት ናት ማለታችን አይደለም። ሰው ሲሞት እንኳን ጥቁር ልብስ እንዳይለበስና እንደ ተሰሎንቄ ሰዎች ከገደብ ያለፈ ክፉኛ ሐዘን እንዳናዝን ቤተክርስቲያን ታዛለች። ጠቢቡ ሰለሞን ቦ ጊዜ ለኩልክሙ // ለሁሉ ጊዜ አለው እንዳለ በቀራንዮ እያነቡ እየሰገዱ ለመዘመር ጊዜ አለው ፤ ይህም በቤተክርስቲያናችን ሰሞነ ሕማማት ይባላል። በብርኃነ ትንሣኤው እንደ መላዕክቱ ብርኃንን ለብሶ ጧፍ ይዞ እልል ብሎ ለመዘመርም ጊዜ አለው።

ስንከፋ ቤተክርስቲያን እንሮጣለን፤ ስንደሰትም ወደ መቅደሱ እንገሠግሣለን። ዳዊት ሲደሰት ብቻ አልነበረም የሚዘምረው። አልጋዬን በእንባዬ አጥባለሁ እያለ እያነባ ይዘምራል። ጸሎቱ ሲሰማ ደግሞ ጩኸቴን ሰማኝ እያለ እልል እያለም ይዘምራል።

ፕሮቴስታንት ዘመዶቻችን ሆይ ዳዊት ጸሎቱ ሲሰማ ልቡ ደስ ደስ ብሎት የዘመረውን ዝማሬ ስሙ፦
መዝሙረ ዳዊት 30
11 ክብሬ ትዘምርልህ ዘንድ ዝምም እንዳትል ((ልቅሶዬን ለደስታ ለወጥህልኝ፥ ማቄን ቀድደህ ደስታንም አስታጠቅኸኝ))

መዝሙረ ዳዊት 81
1 በረድኤታችን በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ፥ ለያዕቆብም አምላክ እልል በሉ።
2 ዝማሬውን አንሡ ከበሮንም ስጡ፥ ደስ የሚያሰኘውን በገና ከመሰንቆ ጋር

እመቦ ዘይተክዝ ለይጸልይ ወእመቦ ዘተፈስሃ ለይዘምር // ያዘነ ቢኖር ይጸልይ ደስም ያለው ይዘምር የታመመ ቢኖር የቤተክ ቀሳውስትን ይጥራና ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት። /ምስጢረ ቀንዲል/ ኃጢአት ሰርቶም ከሆነ ይሰረይለታል //ምስጢረ ንስኃ/ ያዕቆብ 5፦13 ይህን ሁሉ አስተባብራ የያዘች አንድ እናት ቤተክርስቲያን አለች!