Saturday 26 May 2012

“ዕርገት”


ሙሴ አሮንንና ሖርምን ከተማዋን እንዲጠብቁ አድርጎ ኢያሱን አስከትሎ ወደ ደብረ ሲና ሔደ። ኢያሱን ከተራራው ግርጌ ትቶ ሙሴ ብቻውን ወደ ሲና ወጣ። በሲና ተራራም 40 ቀንና ለሊት ቆየ።

በዚህን ጊዜ እስራኤላዊያን ተስፋ ቆረጡና ማጉረምረም ዠመሩ።ፀሐይ ወጣች ገባች ሙሴ ግን ቀለጠአሉ። አመሌ አመሌ ሲል በደብረ ሲና ያያት እሳት አቃጠለችው እንዴ? ሐመልማሉንስ አላቃጠለች ሙሴን ፈጀችው እንዴ? ይህ ባይሆንም ወደኛ ሲመጣ ባሕረ ኤርትራን ሲሻገር ሰጠመ እንዴ? ብለው አጉረመረሙ።



አንገተ ደንዳና የተባሉት እስራኤላዊያን በሬ አላርስ ሲል አንገቱን እንደሚያደነድን አንገታቸውን አደንድነው ካህኑ አሮንን ሙሴ ስለቀረ አምላክም ስለሌለ ጣኦት ስራልን ብለው ጮኹ። አሮን አሮን ግበር ለነ አማልክተ ዘይሐውሩ ቅድሜነ እያሉ ጣኦቱ ይሰራላቸው ዘንድ ካህኑ አሮንን አቻኮሉት አጣደፉትም። ይገርማል! እኛም አንዳንዴ ካህናቱን የማይገባ ሥራ ስሩ እንደምንላቸው ማለት ነው። ካህናቱን መነኮሳትን ጳጳሳትን ባሕታዊያንን ዓለማዊ ስራ ስሩ እንደምንላቸው እስራኤላዊያንም ካህኑን ጣዖት ስራ አሉት።

አሮን ልቡ ተከፈለ። ጣኦቱን ቢሰራ ከፈጣሪ ሊጣላ ባይሰራ እስራኤላዊያን በድንጋይ ሊወግሩት መኾኑን እያሰበ ልቡ ተከፈለ። በመጨረሻም ዘዴ መጣለት። አፍቃሬ ንዋይ ናቸውና ወርቃችሁን አምጡ ብላቸው ይሰስታሉ ብሎ አሰበ። ይኹን እንጂ በልባቸው ያደረው ሰይጣን እጃቸውን ፈቶ ወርቁን በአሮን እግር አስቀመጡ። ካህኑም መሬት ተቆፍሮ ቢቀበር ጣኦት ይኾናል አላቸው በዚያው ጠፍቶ የሚቀር መስሎት። ግና የተቀበረው ወርቅ በግብረ ሰይጣን አንገቱ ወርቅ ደረቱ ብር እግሩ ብረት የኾነ ጥጃ ኾኖ ወጣ።

እስራኤላዊያንም አምላካችን እያሉ መጮኽ ዠመሩ። ቀን ሲደርስ አንባ ይፈርስ እንዲሉ ሙሴ ከሲና ተራራ የሚወርድበት ቀን ደረሰ። ጽላቱን ከእግዚአብሔር ተቀብሎ 40 ቀን ሙሉ ከሲና ተራራ ግርጌ የነበረውን ትዕግስተኛ ኢያሱን አስከትሎ ወደ ሕዝበ እስራኤል መጣ። ነቢዩ ሙሴ ከሲና ተራራ ላይ የቃል ኪዳኑን ታቦት ይዞ ሲወርድ እስራኤላዊያን ጣኦትን ያመልኩ ነበር፤

ሙሴ ከሲና ተራራ መውረዱ .... ጌታችን ከሰማየ ሰማያት የመውረዱ ምሳሌ ነው።     

ታቦቱ ከሙሴ እጅ ወድቆ ጣዖታቱን ሰባበረ ...... ይህም ጌታችን የዲያቢሎስን እራስ እራሱን የመቀጥቀጡ ምሳሌ ነው። 

ጌታ ስለ ኃጢአታችን በፈቃዱ ሞቶ ሞትን ድል አድርጎ ተነሣበክብርም ዐረገይህም ታቦቱ ከእንደገና በእግዚአብሔር ጣት ተጽፎ ለሙሴ የመሰጠቱ ምሳሌ ነው!!!  ዘፀአት ምዕ. 31-34


ልበአምላክ ዳዊት ለምስጋና አሥሩን ቅኝት ቃኘውና በገናውን አነሳና የጌታን ዕርገት በትንቢት መነጽር አየነና እንዲህ አለ፦እግዚአብሔርበእልልታ ጌታችንም በመለከት ድምጽ ዐረገ ዘምሩ ለአማላካችን ዘምሩ፤ ዘምሩ ለንጉሳችን ዘምሩ። መዝ 45:5 መጽሐፍ አንባቢው ያስተውል! ይላል። የዳዊትን መዝሙር ልብ ብለህ ስማው!  ልበ አምላክ ዳዊት ጌታችን በዐረገ ጊዜእግዚአብሔር ዐረገብሎ ተነበየ። ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ ሲነሣ ደግሞ ምን እንዳለ አስተውልእግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነሳ ተነሣመዝ 77:65


አንድም ንዋየ ኅሩይ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በደሙ ያፀናትን የእግዚአብሔርን ቤተክርስቲያን ጠብቁ አለ; ደሙን በላዕለ መስቀል ላይ ያፈሰሰውን ጌታችንንእግዚአብሔርብሎ ተናገረ ሐዋ20:28



"ዕርገት በደብረዘይት ተራራ"

ጌታችን የዐረገው በደብረዘይት ተራራ ላይ ሲሆን በዚህች ተራራ ላይ ብዙ የወይራ ተክል ስለሚገኝ ተራራው ደብረዘይት ተብሏል።

ጌታችን ከትንሳኤእስከ ዕርገቱ 40 ቀናትለሐዋርያቱ እየተገለጸ ያስተምራቸው ነበር። [ሐዋ. 1:3] ነገር ግን ምን እንዳስተማራቸው አልተጻፈም; በመፅሐፈ ኪዳን ላይ ግን ተፅፏል። ቤተክርስቲያናችን አዋልድ መጽሐፍትን የምትጠቀመው በእንዲህ ሁኔታ ነው ማለት ነው።

ይህ ወደ ሰማይ ሲያርግ የአያችሁት ኢየሱስ በክብር ወደ ሰማይ ሲወጣ እንዳያችሁት እንዲሁ በክብር ይመጣልሐዋ. 1:11


አምላክ በእልልታ እግዚአብሔር በመለከት ድምጽ

        *********  ዐረገ    *********  መዝ46:5


      ከላይ እንዳየነው እንደ ልቤ የተባለለት ዳዊት; ብርሐነ ዓለም የተባሉት ሐዋርያት እንዲህ ብለው የጻፉትን መናፍቃኑ ሁሌ ባነበቡት ቁጥር እስከ ዛሬ ድረስ እንዲሁ አይናቸው እያነበበ ያልፉታል!!  ለነገሩ ሐዋርያው አስቀድሞ እንዲህ ብሏል፦እናንተ የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ በመስቀል ላይ የተሰቀለውን ክርስቶስን እንዳታዩ ማን አዚም አደረገባቹገላትያ 3:1

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት ከመጽሐፍ ቅዱስ ከብዙ በጥቂቱ  
                     

ብሉይ ኪዳን ***              አዲስ ኪዳን
መዝ 46:5   ***            ሮሜ 9:5
ኢሳያስ 9:6  ***             እብራዊያን 1:10
ሚክያስ 5:2  ***             ቆላስይስ 1:15
ዘካርያስ 9:9  ***             ራዕ 22:12



            ከዕርገት በኋላ 10ኛዋ ቀን

እመቤታችን ከሐዋርያቱ ጋር በተዘጋ ደጅ ኾና በፀሎት ትረዳቸው ነበር፤ በፀሎት ላይ እያሉም ጌታችን ከሞት በተነሣ 50ኛው በዐረገ 10ኛው ቀን መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያቱ ወረደ። ይህች ቀን ልደታ ዘቤተክርስቲያን በመባል ትታወቃለች፤ ምክንያቱም እነ /ጴጥሮስ በአንድ ቀን 3 ሰዎችን አጥምቀው አማኞች ስላደረጉ ነው። [የሐዋ.2:41] በዚህች ቀን ርደተ መንፈስ ቅዱስ [የመንፈስ ቅዱስ መውረድ ኾኖ ለሐዋርያቱ በአውሎ ንፋስና በእሣት አምሳል ተገለፀላቸው። ጌታችን ለኒቆዲሞስ መንፈስ ቅዱስ በአውሎ ንፋስ መገለፁን ሲያስረዳው እንዲህ አለው፦ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔርን መንግስት አይገባም… “ንፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል ድምፁንም ትሰማለህከየት እንደመጣና ወዴት እንደሚሔድ አታውቅም የተባለውም በዚሁ ምክንያት ነው፤ ዮሐ. 3:8

            ከበዓለ ዕርገት ጋር በተያያዘ ጥያቄ ልናነሳ እንችላለን፤ ብዙ ጊዜ ሰዎች ጌታችን 40 ቀን ብቻ ጾሞ እኛ ለምን 55 ቀናት እንፆማለን እያሉ ይጠይቃሉ፤ ለጥያቄያቸው እራሱን የቻለ መልስ ቢኖረውም ይህን የሚጠይቁ ሰዎች ግን ከትንሣኤ ጀምሮ ሐዋርያቱመንፈስ ቅዱስ  እስከተቀበሉበት ቀን ድረስ 50 ቀናት ለምንድን ነው የማንጾመው ብለው አይጠይቁም፤ ሙሽራው ከሐዋርያቱ ጋር እያለ አይጾሙም ስለተባለ በእነዚህ ግዜያት አይፆምም አይሰገድም ለንስኃ ቀኖና ቢሰጥም ቀኖናው በዚህ ወቅት አይፈጸምም።

[ንስኃ እንገባለን ነገር ግን ቀኖናው  እስከ ጾመ ሐዋርያት ድረስ ይቆያል ]


ዕርገትና እግዚኦታ በእግዚኦታ ላይ ካህኑ ሕብሥቱን ይበልጥ ከፍ አድርጎ ይይዘዋል ይህምየዕርገቱምሳሌ ነው። ከካህኑ ጋር ሆነን 41 ግዜ  እግዚኦ መሐርነ ክርስቶስ እንላለን ይህም አርባው እግዚኦታ አይሁድ ጌታችንን 40 ግዜ እንገርፋለን ብለው እያዛቡ ብዙ ግዜ የመግረፋቸው ምሳሌ ሲሆን በመጨረሻ ካህኑ ብቻውን የሚላት እግዚኦታ ደግሞ የአዳምና የሔዋን የንስሃ ምሳሌ ነው። 12 ግዜ እግዚኦ መሐርነ ክርስቶስ ስንል ደግሞ ስለስምህ ብለህ ይቅር በለን ስንል ነው።

አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስየሚለውን እያንዳንዱን ፊደል ስንቆጥር 12 ይሆናልና!!

Ascend in to haven in glory sit the right hand of the father & again wilt come on glory to judge the quick and the dead Have mercy up on us.

አቤቱ ሞትህን ልዩ የምትሆን ትንሣኤህንም እናስተምራለን፤ ዕርገትህን ዳግመኛ መምጣትህን እናምናለን እናመሰግንሃለን፤ እናምንሃለን
ፈጣሪያችን ሆይ እንማልድሃለን።


በሥጋ የተገለጠ፤
በመንፈስ የተረዳ፤
ለመላዕክት የታየ
በአሕዛብ ዘንድ የተሰበከ፤
በዓለም የታመነ፤
በክብር ዐረገ 1 ጢሞ 3:16

*********

እነኾ በዓለ ዕርገትን ይህን የመሳሰሉትን እያሰብን እናከብራለን። እንዲሁ በዓለ ጰራቅሊጦስን ከመፅሐፍ ቅዱስ እያመሳከርን እናየዋለን።  ለሳምንት ይቆየን!


Visit this Blog! http://yonas-zekarias.blogspot.com/