Saturday 10 December 2011

ነገረ ማርያም [Mariology]


+++ አዳም ዕፀ በለስን ከበላ በሗላ ዕፀ ሕይወት [the tree of life] ነበረለት; ከዕፀ ሕይወት ቢባላ ኖሮ ሞት ሞት የሌለባትን ሕይወት በኖረ ነበር፤ ነገር ግን ከዕፀ ሕይወት አልበላም ለምን ቢሉ እሳታዊያን መላእክት የሆኑት ኪሩቤል በነበልባላዊ ሰይፋቸው ዕፀ ሕይወትን ይጠብቋት ነበርና ይለናል ዘፍጥረት 3:22። ታሪኩን ብናነበው በጣም ደስ ይላል፦ አዳም እጁን ዘርግቶ ከዕፀ ሕይወት ሊበላ ስላልቻለ በላብህ ደክመህ ኑር ተብሎ ከገነት ተባሮ ለእንስሳት ወደተፈጠረችው ወደዚህ አለም ተጣለ። *በመጨረሻው ዘመን ተስፋሁ ለአዳም የተባለችው እመቤታችን ዕፀ ሕይወትን ለአዳም ወለደችለ...ት; ዕፀ ሕይወት ማን ነው ቢሉ ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው ያለን ጌታችን ነው። (ዩሐ. 6: 54) አንድም ዕፀ ሕይወት ማን ነው ቢሉ እኔ የወይን ግንድ ነኝ ያለው የሕይወት እንጀራ ጌታችን ነው። (ዩሐ. 15:5)


*ዕፀ ሕይወት የምትባለዋ የሕይወት ዛፍ መዓዛዋ ከአፍንጫ ጣእሟ ከምላስ ሳይጠፋ ለ7 ቀን የምትቆይ ግሩም ዛፍ ስትሆን ቅጠሏም እንደሌሎቹ አትክልት አይጠወልግም; ይህች ዕፀ ሕይወት አማናዊውን ዕፀ ሕይወት ክርስቶስን በወለደችልን በእመቤታችን ትመሰላለች; ቅጠሏ እንደሌሎቹ አትክልት አለመጠውለጉም የድንግልናዋ ምሳሌ ነው። በዚህም ምክንያት የሶርያ ፀሐይ የተባለው ቅ/ኤፍሬም እመቤታችንን እንዲህ ብሎ አወደሳት፦
“አንቲ ውእቱ እሙ ለዕፀ ሕይወት ወእሙ ለብርሃን”
[O St Mary you are the mother of the tree of life & the mother of luminous light]

ኢትዮጲያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም እንዲህ እያለ በውብ ዜማ አመሰገናት

«ኦ ርህርተ ህሊና እንተ ኤልያስ ደመና ወለተ እያቄም ወሃና
ማርያም ንጹህ ወህብርት በቅድስና
ሶበ ነጸረኪ ሙሴ በሲና
እትምት በድንግልና አልባቲ ሙስና»

ለውሻ እንኳን ያዘንሽ የዋህት ርግብ

ኤልያስ በጸሎቱ 31/2 ዓመት ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን ከዘጋ በኋላ ዝናብ እንዲዘንብ ያደረገብሽ አንቺ ታናሽ የኤልያስ ደመና [1ነገስት 18: 43]

*ሙሴ በደብረ ሲና ያየሽ የሲና ሐመልማል ይላታል ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ


አንድም እግዚአብሔር ለሙሴ ከወርቅ በተሰራ መሶበ ወርቅ ውስጥ መና እንዲያስቀምጥ አዘዘው፤ ይህ መና ለብዙ ዘመን ከዘመነ ሙሴ እስከ ዘመነ ሥጋዌ ሳትበላሽና ሳትሸት ኖረች; ጌታችን በማህጸነ ድንግል ማርያም ባደረ ግዜ ግን ይህች መና እንደሰም ቀልጣ ጠፋች፤ አማናዊው ሕብስተ መና ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ከእመቤታችን ተወልዷላና። እኛም በውዳሴ ማርያም ላይ የተሰወረ መና ያለብሽ ደብተራ ድንኳን አንቺ ነሽ… የምስራቅ ደጃፍ የብርሃን እናቱ ላንቺ ምስጋና ይገባሻል እያልን እንዳመሰገናት።

እምነ ፅዮን ይብል ሰብ [ሰው ሁሉ እናታችን ፅዮን ይላታል] መዝ86:5
የእመቤታችን ፀጋ የፀጋ ልብስ ይሁንልን ፤አሜን [ተክለ መድህን]


ዕፀ ሕይወት [ዘፍ. 3:22]

ሁሉን አሳልፎ ለዚች ቀን ላበቃን
ቸሩ አምላካችን እግዚአብሔር ይመስገን።


እስኪ እንናገረው የአየነውን ነገር
እግዚአብሔር ፈቅዶልን ለዚህ ቀን ካበቃን
እስኪ እንናገረው የድንግልን ተዓምር
ከልብ ለማይጠፋው እጅግ ታላቅ ነገር
ስሟን ስንጠራ ተስፋ ለሆነችን
ተስፋሁ ለአዳም ለሆነችው ድንግል።


አዳም እየኖረ በብዙ እጽዋት በተዋበች ገነት
ይህችን ዕፀ በለስ አትብላ ተባለ ትእዛዝ ሊያከብርባት
አዳም የሞት ሞትን ሞተ ያቺን ዕፀ በለስ ቀጥፎ ስለበላት


አዳም ሆይ! እስኪ እንጠይቅህ
ከዕፀ በለስ በልተህ እንዴት አልበላህም ከዛች ዕፀ ሕይወት?
ብትበላማ ኖሮ ያቺን ዕፀ ሕይወት።
ሞት ወደ ዚህች ዓለም ባልመጣችም ነበር

በዘፍጥረት ምዕራፍ 3 ላይ እንደምናነበው ዘፍ3:22
አዳም እንዳይበላት ያቺን ዕፀ ሕይወት
ትጠበቅ ነበረ በነበልባላዊ ሰይፍ በኪሩቤል መላዕክት
አዳም ሃዘን ገባው ያቺን ዕፀ ሕይወት አይቶ እየናፈቃት
ከገነት ሲወጣም ፅኑ ሃዘኑ በዛበት
ተስፋሁ ለአዳም እሙ ለዕፀ ሕይወት
ጌታን ወለደችው ፤ አዳም የናፈቀውን ያንን ዕፀ ሕይወት
አዳምም ደስ አለው ይህን ዕፀ ሕይወት በልቶ፤ ገነትን ሲያገኛት።


እስኪ እንናገረው የድንግል ተዓምር
በአይን የታየውን ያንን ታላቅ ነገር
አሥሩን አውታር ቃኘውና ዳዊት አባትሽ ለምሥጋና
በገናውን አነሳና ልጄ ሆይ ስሚኝ አለና
እምነ ፅዮን ይብል ሰብ አለና ዘመረ መዝ86:5


የአባቱን በገና እየሰማ አድጎ
ጠቢቡ ሰለሞን እህቴ ርግብየ እያለ
ወትረ ግዜ ድንግል የታጠረች ገነት
የታተመች የውሃ ጉድጓድ ናት አለና ዘመረ። መሓልየ4:12


እስኪ እንዘምር ስለድንግል ክብር
ፅዮን ለተባለች ለዳዊት በገና ለሰለሞን ጥበብ


ጎሳ ልብየ ቃለሰናየ እሙ ለዕፀ ሕይወት እያሉ
እንዳመሰገኗት እነ አባ ሕርያቆስ፤ የሶርያው ፀሐይ እነ አባ ኤፍሬም


እስኪ እንዘምር ጌታን ለወለደች ለእመቤታችን
“እሙ ለዕፀ ሕይወት” የያሬድ ውብ ዜማ እያልን።


ወ ሥ በ ሐ ት ለ እ ግ ዚ አ ብ ሔ ር
/ተክለ መድህን/




ከዓባይ ጋር ኢንተርቪው



«ወይ ዓባይ ኢትዮጵያ ውስጥ ባሕታዊ ነኝ ብለህ በረሃ ለበረሃ፣ ሸለቆ ለሸለቆ ስትመንን የኖርክ ወንዝ እዚህ ካይሮ መጥተህ ከተሜ ትሆን? እንዴው ምን ቢያቀምሱህ ነው እንዲህ የከተማ ወንዝ የሆንከው ጃል አልኩት ካይሮ ላይ ዓባይን ሳገኘው፡፡

«ከሀገሩ ሲወጣ ምናኔውን ብሕትውናውን ያልተወ ማን አለ? እህል አንቀምስም፣ ልብስ አንለብስም፣ ጫማ አናደርግም፣ ሬዲዮ አንሰማም፣ ሰዓት አናሥርም ሲሉ የነበሩት ሁሉ ውጭ ሀገር ወጥተው አይደለም እንዴ ከተሜ ሆነው የቀሩት? ምን በኔ የተጀመረ ታስመስላለህ

«ቆይ ግን አንተ ይህንን ያህል ዘመን ኖረህ ኖረህ ዛሬ ልትገደብ መሆኑን ስትሰማ ምን ተሰማህ

«በርግጥ ደስ ይላል፡፡ እነ ዐፄ ሐርቤ፣ እነ ዐፄ ዳዊት ያሰቡት ሲሳካ ማየት እንደገና መወለድ ነው፡፡ አይተህኛል ካይሮ ላይ፡፡ ወንዝ ሆኜ እገማደላለህ፣ ኩሬ ሆኜ ዕታቆራለሁ፣ የቦይ ውኃ ሆኜ መንደር ለመንደር እዞራለሁ፣ የመስኖ ውኃ ሆኜ ገጠር ለገጠር እንከራ ተታለሁ፡፡ የቧንቧ ውኃ ሆኜ ቤት ለቤት አዞራለሁ፡፡ የቆሻሻ መውሰጃ ሆኜ ቱቦ ለቱቦ እሰቃያለሁ፡፡ ምን ያልሆንኩት አለ፡፡»

«እናንተ ሀገርስ ዘፈን ብቻ ሆኜ ቀረሁ፡፡ ተረት ሆኜ ቀረሁ፡፡ አሁንም እንኳን ትተርቱብኛላችሁ አሉ፡፡»

«ምን ብለን የማይሆን ነገር ሰምተህ እንዳይሆን

«ዓባይ ማደርያ የለው ቦንድ ይዞ ይዞራል ትላላችሁ አሉ፡፡ ምናለ እንኳን ዓባይ ማደርያ ሊያገኝ ቦንድ ይዞ ይዞራል ብትሉት፡፡»

«አንተምኮ አበዛኸው፡፡ ገና ከጣና ከመውጣትህ እንዴው ገደል ለገደል ዝንጀሮ ይመስል ስትጓዝ ሰንብተህ ከሀገር ትወጣለህ፡፡»

«ሰው ለምን በረሃ እንደሚገባ፣ ለምን ገደል ለገደል እንደሚሸፍት ታውቃለህ? ሲከፋው እኮ ነው፡፡ አልመች ሲለው፡፡

ዓባይ ጉደል ጉደል ቀጭን መንገድ አውጣ
የከፋው ወንድ ልጅ ተሻግሮ እንዲመጣ
ትሉ የለም፡፡ እኔምኮ ከፋኝ፡፡

«ለምን
«ካይሮን አይተሃታል? እኔን ስንት ቦታ ነው የከፋፈሉኝ፡፡ ከኔ አጠገብ ቤት የሚሠሩኮ ሀብታሞች ናቸው፡፡ መርከቡ፣ ጀልባው፣ መዝናኛው፣ መናፈሻው ኧረ ስንቱ ሲገማሸልብኝ ይውላል ያመሻል፡፡ እስኪ ባሕርዳር ከተማን ሄደህ እያት፡፡ ለመሆኑ ዓባይ በዚያ የሚያልፍ ይመስላል፡፡ ገና ከጣና ስወጣ ፋብሪካ ገትራችሁ ቆሻሻ ትለቁብኛላችሁ፡፡ ደግ ነገር የጠፋ ይመስል ጅኒ፣ ዛር፣ ጋኔን የተሰበሰበብኝ አድርጋችሁ ነው የምታወሩት፡፡ እየዘለለ የገባውን ሁሉ ዓባይ ስቦት ነው ትላላችሁ፡፡

«አየህ ካይሮ ላይ የምጓዝበትን መንገድ ግራ ቀኙን አስተካክለው ጥልቀት እንዲኖረው አደረጉና መርከብ ነዱበት፡፡ አሁን ባሕርዳር ላይ እንዲህ ቢደረግ ምን ነበረበት? ጣናን አንድ ነገር ሳትሠሩ ከጥግ እስከ ጥግ ሻሂ ቤት አድርጋችሁት ቀራችሁ፡፡ እስኪ አንድ የመርከብ ላይ መዝናኛ አለ? እስኪ ምናለ ከተማዋን ወደ ምዕራብ ከመለጠጥ ወደ ምሥራቅ ወስዶ እኔን መካከል ብታደርጉኝ?

«እናም ከፋኝ ጥዬ ሄድኩ፡፡ ምን ታደርጉ ዋናው ከተማ አዲስ አበባ ውስጥ ከአሥር በላይ ወንዞች ነበሩ፡፡ ግን ምን ሆኑ? የቆሻሻ መጣያ ሆነው ነው የቀሩት፡፡ እኔኮ ምን ሆናችሁ ነው ከውኃ ጋር የተጣላችሁት? የተከራዩን ቧንቧ መዝጋት ነው እንዴ ለእናንተ የውኃ ልማት? ወንዙን አታለሙም? አፍሪካ ውስጥ እንኳን የኒጀር ወንዝ፣ የኮንጎ ወንዝ፣ የዛምቤዚ ወንዝ ያገኙትን ወግ መዓርግ እኔ መች አገኘሁ፡፡ ተወኝ ተወኝ ባክህ ክፉ አታናግረኝ፡፡»

«ይኼው ከትናንት ብንዘገይ ከነገ እንቀድማለን ብለን ተነሣንኮ»

«ባክህ እናንተ ውጭ የሄደ ስለምትወድዱ ነው

«እንዴት ባክህ

«ነዋ እናንተ ሀገር ከውስጥ ይልቅ የውጭ ስለሚከበር ነው፡፡ ምነው ለአዋሽ አትዘፍኑ? አሁን ከእኔ በላይ አዋሽ አላገለገላችሁም? ከእኔ በላይ ለሀገሩ አዋሽ አልሠራም? ችግሩ አዋሽ እና ዋልያ ከሀገር አይወጡም፡፡ እናንተ ደግሞ ሀገር ውስጥ ያለ ነገር አትወድዱም፡፡»

«ኧረ እባክህ የማይሆን ወሬ እየሰማህ አትማረር»

«ነው እንጂ እስኪ አንተ አዲስ ላፕ ቶፕ ይዘህ ግባ? አይቀርጡህም

«ይቀርጡኛል፡፡»

«ግሪን ካርድ ወይንም የውጭ ሀገር ፓስፖርት ያለውን ኢትዮጵያዊስ

«እርሱማ አንድ ከያዘ አይቀረጥም፡፡»

«ለምን

«እንግዳ ተቀባይ ስለሆን ነዋ»

«እንደገና ሞክር»

«ሕጉ ይሆናላ»

«ሕጉ አይደለም አስተሳሰባችሁ ነው፡፡ እዚያው ሀገር ውስጥ ሆኖ ለሀገሩ አስፈላጊውን ሁሉ እየከፈለ ከሚኖረው ይልቅ ከዕለታት አንድ ቀን ብቅ የሚለው ዲያስጶራ ይከበራል፡፡ ከጋምቤላ ከምትመጣ ከካምፓላ ብትመጣ ትከበራለህ፡፡»

«እይውልህ ዓባይ፣ አሁን ሁሉም ነገር አልፎ ሀገር ተነቃንቋል፡፡ ወሬውኮ ዓባይ ዓባይ ብቻ ሆኗል፡፡ ግብፆችን እንኳን አታያቸውም፡፡ ኢትዮጵያን እንጎብኝ ብለው የማያውቁት እንደ ጥንቱ የሕዝብ መዝሙር ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ ብለው ሊሞቱኮ ነው፡፡»

«እሱ እሱንስ ሳይ አንጀቴ ይርሳል፡፡ እዚህኮ ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አያውቁም ነበር፡፡ የመማርያ መጽሐፋቸው ላይኮ ዓባይ መነሻው ግብጽ ነው ብለው የሚጽፉ ደፋሮችኮ ናቸው፡፡ እዚህ ያሉ አበሾች አልነገሩህም»

«ምን

«እዚህ ያሉ ሰዎች ኢትዮጵያን አያውቁም፡፡ ደግሞ ጠባያቸው ሆኖ መንገድ ላይ ሲያገኙህ ሀገርህ የት ነው? ማለት ይወዳሉ፡፡ እና ሐበሾቹ ኢትዮጵያ ነው ሲሏቸው የት ነው? እያሉ ልባቸውን ያወልቁታል፡፡

«እሺ»

«እናም ሲሰለቻቸው ምን እንደሚሏቸው ታውቃለህ

«ከየት ነው የመጣህው»

«ከሽንኩርት፡፡»

«ሽንኩርት የት ነው

«ከድንች አጠገብ»

«ድንችስ የት ነው?»

«ከቃርያ አጠገብ»

«ቃርያስ

«ከዝንጅብል አጠገብ»

«ዝንጅብልስ

«ከጥቁር አዝሙድ አጠገብ»

ሁሉም ነገር አልገባው ሲል «አይ ዋ፣ አይ ዐወቅኩት፣ ዐወቅኩት» ይልና አንገቱን ነቅንቆ ያበቃል፡፡

«ዛሬማ አወቋትኮ ኢትዮጵያን፡፡ ጋዜጦቻቸው ያነሡት ጀመርኮ፡፡ መንገድ ላይ ሲያገኙህ ሐበሻ መሆንክን ሲያውቁ ይጠይቁሃል፡፡ ውኃ ልትዘጉብን ነው አሉ? ይሉሃል፡፡ ኮራሁኮ አሁንማ ሀገሬ ታወቀ፡፡»

« ሁሉ ሕዝብ ግለበጥ ብሎ ደመወዙን ያወጣውኮ ይህንን ሀገራዊ ኩራት ለማምጣት ነው፡፡»

«የሕዝቡ መነሣሣት፣ አንድ ልብ መሆን፣ ቁጭት ልቤን ነካው፡፡ ግን ምን ዋጋ አለው፡፡»

«ደግሞ ምን ልታመጣ ነው

«እይውልህ አንድ አባት ነበረ አሉ፡፡ ለልጆቹ ሀብቱን ለማውረስ ሽር ጉድ ይላል፡፡ ልጆቹ ደግሞ ከአባታቸው ሀብቱን ለመንጠቅ ሽር ጉድ ይላሉ፡፡ አንድ ቀን ለልቅሶ ሌላ ሀገር በሄደ ጊዜ ራሳቸው ቤቱን ሰብረው ሀብቱን በሙሉ ነጠቁና ለሦስት ተካፈሉት፡፡ አባትዬው ሲመጣ ሀብት ንብረቱ የለም፡፡

«በኋላ በአውጫጭኝ ሲጣራ ለካስ ልጆቹ ናቸው የወሰዱት፡፡ አባት ይህንን ሲሰማ እንዲህ አለ ይባላል «መውሰዱንስ ውሰዱት፣ ሀብታችሁ ነው፡፡ ያስቀመጥኩትም ለእናንተ ነው፡፡ የሚያሳዝነኝ ግን መርቄያችሁ ልትወስዱት ስትችሉ ረግሜያችሁ መውሰዳችሁ ብቻ ነው» አለ አሉ፡፡

«ይህ ከአንተ ግድብ ጋር ምን አገናኘው ታድያ?»

«ሕዝቡኮ ልጆቹን «ይገደብ ዓባይ» እያለ ስም ሲሰጥ የኖረ ነው፡፡ መሪ አጥቶ ኖረ እንጂ ገንዘብ አልሰጥም አላለም ነበር፡፡ አሁንም ዓባይ ሊገደብ ነው ሲባል በደስታ ነው የተነሣው፡፡ ታድያ አንዳንዶቹ በፈቃዱ መስጠት የሚችለውን በግዳጅ አደረጉትና ምርቃቱን ወደ ርግማን ቀየሩት፡፡

«እንዴት ዝቅ ብሎ የግማሽ ወር፣ ከፍ ብሎ የሁለት ወር የሚሰጥ ይጠፋል? እንዴት ሁሉም እንደ ኮካ ኮላ ጠርሙስ አንድ ይሆናል? ሕዝቡኮ ሀገሩ ነው፡፡ ይሰጣል፡፡ በራሳችን ገንዘብ እንገንባው መባሉም ልብ የሚያሞቅ ነው፡፡ ግን እወደድ ባዮች ፈቃዱን ወደ ግዳጅ፣ ምርቃቱን ወደ ርግማን እንዳይቀይሩት እፈራለሁ፡፡

« እሷኛዋ በቄላ በጊዜ ካልተከካች ልክነህ አትቆረጠምም፡፡ ግን አንተ ስታስበው ይሄ አንተን የመገደቡ ጉዳይ ጦርነት አያስነሣም ትላለሀ»
«የናንተ ሀገር ካህናት ምን እንደሚሉ ታውቃለህ
«ብዙ ነገር ይላሉ»
«ጅብ ከሚበላህ በልተህው ተቀደስ»



“የዲያቆን ዳንኤል ክብረት እይታዎች”