Friday 27 January 2012

             የእናታችን ወተት ያስፈልገናል በሉ”!

ዘና ብላችሁ ተቀመጡና እስኪ ገጠመኜን ላውጋችሁ፤
የዛሬው ገጠመኜ ካለሁበት ከተማ ከለንደን ነው ፤
ግዜው የፈረንጆቹ ሰመር ነበርና የጠዋቷ ፀሐይ ፈካ ብላ ወጥታለች። የከተማዋ ሰዎችም እድለኛ ናቸውና ብዙ የመዝናኛና የእስፖርት መለማመጃ ትላልቅ ፓርኮች አሏቸው። ብዙዎቹ የፀሐይ መከላከያ መነፅራቸውን በቄንጠኛው አድርገው በየሜዳው ተዘርረዋል፤


ከአጠገባችን የተቀመጡ ሰዎች በእጃቸው ላይ የያዙትን መፅሐፍ ቅዱስ ገልጠው ይወያያሉ፤ በተወሰኑ ወጣቶችም ተከበዋል። እኛም ለማየት ያህል ቀረብ አልን፤ በመጀመሪያ ጆሯችን የገባው “ወንጌል አንዲት ናት እናንተ ግን ገድል ተዓምር እያላችሁ ብዙ መፅሐፍ አላችሁ; ይህን ሁሉ ከየትኛው ወንጌል አምጥታችሁ ነው የፃፋችሁት” የሚል ነበር።
    


ከመካከላችን አንዱ ጥያቄውን በጥያቄ መለሰላቸው፤
ጥያቄያችሁን ለመመለስ ያህል ወንጌላዊው ማቴዎስ እንዲህ ይልላችኋል አለና ከሞባይሉ ላይ የጫነውን ማስታወሻ አነበበላቸው፦ በነብያት ናዝራዊ ይባላል ተብሎ የተነገረው ይፈፀም ዘንድ ናዝሬት ወደ ምትባል ከተማ ገብቶ ኖረ” [ማቴ. 2: 23] ይህን ካነበበ በኋላ ቀና ብሎ አየና እንዲህ ብሎ ጠየቃቸው፦

ናዝራዊ ይባላል ብሎ የተነበየው ነብይ ማን ነው? በየትኛው ትንቢት ላይስ ይገኛል?

ግሞሾቹ ዝም አሉ ሌሎቹም ከማስታወሻቸው ፈለጉ፤ አንዱ ግን ከኋላ ሆኖ መፅሐፍ ቅዱስ ሲያገላብጥ አየው።

ብዙ አትድከሙ ይህን ትንቢት በመፅሐፍ ቅዱስ ከዘፍጥረት እስከ ራዕይ ብትፈልጉት አታገኙትም! እነሆ ነብያቱ “ናዝራዊ ይባል ዘንድ ናዝሬት ወደ ምትባል ከተማ ገብቶ ኖረ ብለው ተንብየው ነበር፤ ይህ ትንቢት በነብያት ተነግሮ በምርኮ ግዜ በጠፉት መጻሕፍት የነበረ ሲሆን መጽሐፍቱ ቢጠፉም በቃል ለሐዋርያት ደርሷል። እነሆ ማቶዎስም በወንጌሉ ፃፈው!

አንድም ሙሴን የተቃወሙትን ጠንቋዮች ስማቸውን አልነገረንም፤ ቅ/ጳውሎስ ግን ኢያኔስና ኢያንበሬስ” ብሎ ስማቸውንም ጭምር ተናግሯል [2ኛ ጢሞ. 3: 8] ማን ነገረው? እነሆ በትውፊት ያገኘውን ተጠቅሞ ታላቁ ሐዋርያ በመልዕክቱ ላይ ጽፎታል።

አንድም ቅ/ጳውሎስ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ለተግሳጽና ለምክር ያስፈልጋሉ ብሎ ለጢሞቴዎስ አስተምሮታል [2ኛ ጢሞ. 3: 15] ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስ አንዴ በተግባር አንዴ በመልዕክቱ እየፃፈ ስለ አዋልድ መፅሐፍት ጢሞቴዎስን አስተምሮታል።

አንድም ሐዋርያው ይሁዳ ስለ ቅ/ሚካኤልና ስለዲያቢሎስ ክርክር በመልዕክቱ ላይ ይነግረናል [ይሁዳ 1:8] ይህ ክርክር ግን በመፅሐፍ ቅዱስ ላይ አልተፃፈም ፤ ታዲያ ሐዋርያው ይሁዳ ይህን ታሪክ ከየት አምጥቶ ነው የፃፈው?

እነሆ ታሪኩ እንዲህ ነው፦  ሊቀ ነብያት ሙሴ እጅግ ታዛዥና የዋህ ስለነበር ሀገረ ከንዓንን ለማየት ወደ ናባው ተራራ በወጣ ግዜ ሁለት መላዕክት በአረጋውያን ተመስለው መቃብር ሲቆፍሩ ሲያይ ላግዛቹ ብሎ መቆፈሪያውን ተቀበላቸው፤ እነሱም በመጨረሻ “ሰውየው በአንተ ልክ ነውና እስቲ ገብተህ ለካልን አሉት  እሱም በየዋህነቱ ጉድጓዱ ውስጥ ገብቶ እንደተኛ እንደ እንቅልፍ አሸልቦት በዚያው ዐረፈ; መላዕክትም ቀበሩት። እስራኤላዊያን ሙሴን እጅግ ስለሚወዱት የሙሴን መቃብር እንደ ጣዖት እንዳያመልኩት እግዚአብሔር የሙሴን መቃብር ሰወረው፤ ነገር ግን ጠላት ዲያቢሎስ ሊያሳያቸው በመነሳቱ ቅዱስ ሚካኤል ተቃወመው; በመጨረሻም ቅዱስ ሚካኤል ዲያቢሎስን እግዚአብሔር ይገስጽህ ብሎ ከራሱም ሰወረበት።

ሐዋርያው ይሁዳ ይህን ታሪክ ያገኘው እርገተ ሙሴ ከሚባለው የትውፊት መፅሐፍ ነው።
Source፦ the Assumption of Moses
የሐዋርያው ይሁዳ መልዕክት
ቁጥር 8

እነሆ ቤተክርስቲያንም ሐዋርያት እንዳስተማሯት እኛን ታስተምረናለች! አለንና ወደ ኋላው ዞር እያለ “ታዲያ በዚህች ቤተክርስቲያን አትኮሩም እንዴ”? ብሎ ጠቀየቀን፤ ሁላችንም ኧረ እንኮራለን” ብለን መለስንለት። የደስታ ስሜት ተነበበበትና እኔን የሚገርመኝ ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? አለን ጓደኛችን፤

ምን ገረመህ”? አልነው በልባችን፤
እንዲህ ብሎ ቀጠለልን፤

እኔን በጣም የሚገርመኝ ባሕረ ጥበብ የሆነችው ቤተክርስቲያን እያንዳንዱ ሥርዓትዋ በሚስጢር የተዋቡ መሆናቸው ነው! ኧረ ሰዎች ይህችን ጥበበኛ እናት በደንብ እንወቃት፤ ከጣራ እስከ ግድግዳዋ ያስተምረናል። እኛ ለማወቅ እንፈልግ እንጂ ይህች እናት እንደዘመኑ ሴቶች የተፈጥሮ ወተትን ነፍጋን አርቴፊሻል ወተት አትግተንም!

ከላም ወይም ከሌሎች የወተት አይነቶች ይልቅ የእናት ወተት ለህፃኑ ጠቃሚ ነው፤ በተለይ እናትየው በመጀመሪያ የምታጠባው ወተት ማለትም እንገር /colostrums/ የሚባለው ለህፃኑ ጤንነትና እድገት እጅግ ወሳኝ ነው። እኛም ከእናታችን ቤተክርስቲያን የመጀመሪያውን ወተት በጥምቀት አማካኝነት ተመግበናል። ይህ ልክ እንደ ህፃኑ ለጤንነታችንና ለእድገታችን እጅግ ወሳኝ ነው!

ደግ የሆነች እናት ቤተክርስቲያን አለን፤ ወተትዋን ለማጥባት የማትሰለች ደግ እናት! ጥምቀቱ ወተት ነው ልጅነትን ያሰጣልና፤ ቁርባኑ ወተት ነው ከኃጢአት ያነፃናልና፤ ተክሊሉ ወተት ነው የትዳራችን ውበት ነውና፤
ትምሕርቷ ሁሉ ግሩም ወተት ነው ያውም ለጤንነትና ለእድገት ወሳኝ የሆነ ጣፋጭ የእናት ወተት።

የእናታችን ወተት ያስፈልገናል በሉ”!