Saturday 11 August 2012




ሮጥ እንደዚህ ነው በአንድ ላይ ተባብሮ
ም እና ወርቁ በአንድ ተጨምሮ
ጅም ሩጫን አየነው ዘንድሮ!
ምህርትም ሆነን ለመስራት ተፋቅሮ

ፋር ነች ጀግና ነች እውነትም ደፋር ነች
ታ አልሰጠችም ልክ እንዳሸነፈች
ግብዬ ብላ እመቤቴን ያዘች!

እልል ይበሉ የወለዱ እናትሽ
ያኔ እንደተባለው አምጠው ሲወልዱሽ
ጋሻና ጦር ያዙ ፎክሩ በሏቸው
ዘራፍ! የጀግና ልጅ! ይበሉ ደፋሩ አባትሽ!!!













ደፋር ነሽ ጀግና ነሽ እውነትም ደፋር ነሽ
እጅግ ይደሰቱ የወለዱ አባትሽ
ደፋር ነው አባትዋ ልጅቱም ደፋር ናት
አሯሯጧን ያየ በአባትዋ የወጣች “ደፋር ናት” የሚላት

ደፋር ነሽ ጀግና ነሽ እውነትም ደፋር ነሽ
እጅግ ይደሰቱ የወለዱ እናትሽ

ደፋር ነሽ ጀግና ነሽ እውነትም ደፋር ነሽ
ይህን ድንቅ ስምሽ ማን ይሆን የሰጠሽ!







ሱባኤውን ይዘሽ ፍልሰታንም ጾመሽ
ድንግል እናትሽን ከደረትሽ ይዘሽ
ወላዲተ አምላክ እርጂኝ ብለሽ ለመንሽ
እልልልል ይኸው ተሳካልሽ
ታላቅ እምነትሽን በዓለም ላይ ሰበክሽ!


ደፋር ነሽ ጀግና ነሽ እውነትም ደፋር ነሽ
ድፍረት ከእምነት ጋር ፈጣሪ ለገሰሽ
መሰረት እስኪ ልጠይቅሽ
ምነው ቪቪያንን ጥለሽ ብቻሽን ገሠገሥሽ?
"
ብቻውን የሮጠ ማንንም አይቀድምም"
ብቻሽን ሮጠሽ ብቻሽን አልበላሽ
መሠረት ጥሩነሽ ገለቴ ምን ልበል በሞቴ?
ፍቅር አንድነትን ህብረት መቻቻልን
እስኪ አስተምሩን ለሀገር መስራትን
"
ብቻውን የሮጠ ማንንም አይቀድምም"
ብለው አስተማሩን ድንቅ ወርቆቻችን!







ደፋር ነሽ ጀግና ነሽ እውነትም ደፋር ነሽ
ሩጫን አስተማርሽ አፈትልከሽ ሮጠሽ!
ነይ ተደሰቺ ባንዲራውን ይዘሽ
ሽልማትሽ ይህ ነው ለፈሰሰው ላብሽ!

እልል ይበሉ የወለዱ እናትሽ
ያኔ እንደተባለው አምጠው ሲወልዱሽ
ጋሻና ጦር ያዙ ፎክሩ በሏቸው
ዘራፍ! የጀግና ልጅ! ይበሉ ደፋሩ አባትሽ!!!










                                              
                                        
 ይድረስ ለታላቅዋ        


              የእምነት ሰው
     
          
                         መሠረት ደፋር!





ETV (DVD)

ዘና ብላችሁ ተቀመጡና አንድ አሪፍ ታሪክ ላውጋችኹ!

ሹርባ ልትሰራ ሄዳ ጸጉሯን ተላጭታ መጣች” አሉና ”አምራለሁ ብላ ተኩላ ዓይኗን አጠፋችው ቸኩላ” አሉ እትዬ ጣይቱ ውብ ሴት ልጃቸውን እየመከሩ። ልጅቱም በእናትዋ ወጥታ ኖሯል ጀንበር ካለች እሩት እናት ካለች አጊጥ” አለቻቸው።

የእለቱ ኢቲቪ ዝግጅቶቻችን እነዚህ ናቸው።

ዜና፦ ሲባዛ በመቶ (DVD)

ማስታወቂያ፦ ሲባዛ በመቶ (DVD)

ድራማ፦ሲባዛ በመቶ (DVD)

አጠር ብለው ረዘም ያሉ ንግግሮች፦ ሲባዛ በመቶ (DVD)

ፕሮግራሙ ሁሉ “በ DVD” ናቸው።

የሰለጠነው ዓለም ማንም የፈለገ ባለሥልጣን ቢሆን ከአጭር ደቂቃዎች በላይ የቴሌቭዥን የአየር ጊዜ አይሰጠውም። እኛ ቤት ግን አንድ የቀበሌ ኃላፊ አጠር ብላ ረዘም ያለች ታሪክ ይተርክልናል። ይህ እኛ ቤት ነው። በሰለጠነው ዓለም ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንኳን መግለጫ ቢሰጡ እንደ እኛ አጠር ብላ ረዘም ያለች ሳትኾን በቃ! አጠር ያለች ናት። ትሻልን ትተሽ ትብስን አመጣሽ” አሉ እትዬ ጣይቱ! ይባስ ብለው የወንዶቹ አስር ሺህ ፍጻሜ ካለቀ በኋላ ኢቲቪ ስንከፍት ክቡራን ተመልካቾቻችን ውድድሩ ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ይጀመራል” አሉን። እስከ ዛሬ ድረስ ለካ DVD ነው የምናየው። በኢቲቪ DVD ማጫወቻ የተከተተው DVD ሲያልቅ ከእንደገና ሪዋይንድ አድርገን ጥንት ያለቀውን ሩጫ እንደ አዲስ ማየት እንችላለን። ምን ይህ ብቻ መቶ ጊዜ የሚደጋገመውም ለካ DVD ስለሆነ ነው! በጣም የሚገርመኝ ደግሞ ያቺ በዜና ላይ የምናያት የጋዜጠኞቹ ኮምፒተር ናት። እንደ አርቴፊሻል አበባ ለጌጥ የተቀመጠች ይመስለኛል። አንዳች ትኩስ ነገር ሳይነበብባት ለጌጥ የተቀመጠች አርቴፊሻል አበባ መሆንዋ እኔ ጣይቱ ገብቶኛል። ከትላንት በስቲያ በኦሎምፒክ ቻይና በዘጠኝ ወርቅ እየመራች በስድስት ወርቅ ትመራለች ተብሎ ተነግሮናል። ታዲያ ኮምፒተሩ ስራው ምንድን ነው? የኮምፒተሩ ስራማ DVD ማጫወት ስለሆነ የሚከፈትልንን እናያለን አሉ እትዬ ጣይቱ ገና በጠዋቱ!


እትዬ ጣይቱ ከአዲስ አበባ ለንደን የገቡት በቅርቡ ነበርና ለሳቸው ተብሎ ETV ዲሽ ተገጠመ። የእንግሊዘኛ ፕሮግራም ብዙም ስለማይገባቸው አይጥማቸውምና እስኪ ያችን DVD” ክፈትልኝ አሉ እትዬ ጣይቱ ስልችት ብለው። እኔም በቅርብ ያገኘሁትን DVD ከፈትኩላቸው። እትዬ ጣይቱ ግን ፍግግ እያሉ እዲያ እኔ ያልኩት የኢቲቪን DVD ነው አሉ። እኔም ከትከት ብዬ ሳቅኩና ደግሞ የምን DVD ፕሮግራም ተጀመረ? አልኳቸው። እዲያ ያን የሀገሬን DVD ክፈት አሉኝ እትዬ ጣይቱ ሪሞቱን በእጃቸው እያሳዩኝ። ከዛች ቀን ጀምሮ እትዬ ጣይቱ ባወጡለት ስም መጥራት ጀመርን። ETV ሳይሆን “DVD ብለነዋል።


እትዬ ጣይቱ ከዘራቸውን ደገፍ ብለው በሐሳብ ባቡር ተሳፈሩና እንዲህ እያሉ ታሪካቸውን አወጉኝ። ቢቢሲ ዘወትር ቅዳሜ ከምሽቱ 2 ሰአት ላይ የሚያሳየው ድንቅ ፕሮግራም አለ። ፕሮግራሙ ተፈጥሮ ድንቅ ናት” ይባላል። ተፈጥሮ ከነልጆችዋ ከነውበትዋ እጇን ይዘው ቤታችችሁ ድረስ የመጣች እስኪመስላችሁ ድረስ እጅግ ይመስጣል። የአናብስትና የአራዊቱ ልብ የሚመስጥ ፍጥጫ፣ የዝሆኖች ልፊያ ፣ የዓሦች አክሮባቲክ ድንቅ ችሎታ ልብና ዓይንን ገዝቶ አፍን አስከፍቶ ያስቀራል!


በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዓሦች ሲዋኙ ግርማ ሞገሥ ያለው ሻርክ ይመጣና ይፎክርባቸዋል። ሻርክ በቀን 6 የሚያህሉ ዓሦችን መብላት አለበትና እንደ ጉድ ያራውጣቸዋል!


ዓሦቹም እንደ ጉድ ይራወጣሉ!

እንደ ጉድ በግሩፕ ይከፋፈላሉ!

እንደ ጉድ ነፍሴ አይጪኝ እያሉ ውር ውር ይላሉ!

ሻርኩም የኦሎምፒክ ጅምናስቲክ ውድድር ያለበት ይመስል ለአፌ ጅምናስቲክ የሚሆኑ ዓሦች ካላገኘሁ አላርፍም እያለ እንደ ጉድ ውኃውን በትጋት ይጋልባል! ይህ ሻርክ እንደ ዋና ብቃቱ ከሆነ በኦሎምፒክ ሪከርድ ይሰብራል ተብሎለታል! በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዓሦች በሚሊዮን በሚቆጠሩ ግሩፕ ተከፋፍለው ቀስ በቀስ ብቸኛ ዓሣ ይኾናሉ። ሻርኩም ይህችን ብቸኛ ዓሣ የገባችበት ገብቶ እንደጎመጀው ለአፉ ጅምናስቲክ ያደርጋታል!  ይህች የዕለቱ የመጀመሪያ አፕታይዘር ናት። አቶ ሻርክ ቢያንስ 6 ዓሦችን ካላገኘ የበላ አይመስለውምና ይህን ሂደት እንደገና ይጀምራል……      “ዓሣ የጌቶች ምሳ የገረድ አበሳ” አሉ እትዬ ጣይቱ ፍግግ እያሉ! ወዲያው ፈገግታቸው ከፊታቸው ጠፍቶ እንዲህ እያሉ ብሶታቸውን ቀጠሉ። እነዚያ በተፈጥሮ ውበት ልባቸው የከነፈ ባለሙያዎችም የውኃ ውስጥ ካሜራቸውን ይዘው የውኃን ዓለም እንደ ጉድ ያሳዩናል። ይግረማችሁ ብለው ኢትዮጵያ ገቡና ግሩም ድንቅ ተፈጥሮን አሳዩን! አንድ ትልቅ ንሥር እጅግ ከፍ ካለ በሀገሬ ተራራ ላይ ወጣና በአፉ የያዘውን አጥንት ለቀቀው። ያ አጥንት እየተምዘገዘገ መጣና ዐለቱን መታ። አጥንቱም እዬዬ ብሎ ጮኸ! እንደ ጉድ ደቀቀ! ንሥሩ ክንፉን እያማታ እንደ ጉድ ወደ ታች ተምዘገዘገ! ከአጥንቱ የወጣውን ቦን ማሮው እንደ ጉድ በላ! ከዚያም እንደ ጉድ ክንፉን እያማታ በረረ!


ይህ ነው መዝናኛ ማለት!

ይህ ነው ሊታይ የሚገባው!

ይህን ነው ለማየት መጓጓት!

ዓይን ካላዩበት ግንባር ነው” አሉ እትዬ ጣይቱ ዓይናቸውን ጨፍነው ግንባራቸውን አንዴ ኮስተር አንዴ ፈታ እያደረጉ! እትዬ ጣይቱ ጨዋታ አሳምረው ከማወቃቸውም በላይ ንግግራቸው ሁሉ በእንቅስቃሴ የታጀበ ስለሆነ ነገረ ስራቸው ሁሉ ያስቀናል። የእትዬ ጣይቱ እሮሮ ቀጠለ።  ልብ በሉ ነጮቹ ይህችን እይታ ለሕዝባቸው ለማሳየት ነው ይህን ሁሉ ባሕር አቋርጠው ኢትዮጵያ የመጡት። እኛስ? ኢቲቪዬዋ እንደምን አሉልኝ? እምዬ ኢቲቪ እንዲህ ቢያዝናኑን አሁን ምን ነበረበት? ሁሉን ቢናገሩ ሆድ ባዶ ይቀራል” አሉ እትዬ ጣይቱ ሆዳቸውን በእጃቸው እየዳሰሱ። በእትዬ ጣይቱ ንግግር ኢቲቪ ክፉኛ አኮረፉ። ሆደ ሰፊ ይሻላል ከአኩራፊ ሲባል አልሰሙም እንዴ?” አሉ እትዬ ጣይቱ የተፈጥሮ ሆዳቸውን አየር ምገው ሰፊ እያደረጉ። በቃ! ሆደ ሰፊ ሆነው ስሙኝ። ምን መሰሎት አሁን እሺ እኛ ቤት ስንመጣስ ምን እናያለን? የባለሥልጣናትን አጠር ብለው ረዘም ያሉ ንግግሮችን? አጠር ብለው ረዘም ያሉ ማሳሰቢያዎችን? አጠር ብለው ረዘም ያሉ ውይይቶችን? ለሁሉ ጊዜ አለው አለ ጠቢቡ። አዎ ለሁሉም ቦታና ጊዜ አለው። ለእነዚህ ሁሉ ራሳቸውን የቻሉ ቦታ አላቸው አሉ እትዬ ጣይቱ ገና በጠዋቱ። መናገር መልካም ነው ማዳመጥ ይበልጣል” ብለህ ነው መሰል ዝም ብለህ ትሰማኛለህ፤ በል ተናገር ብዙ ዝምታ ይሆናል በሽታ” ብለው እንደለመዱት በአባባላቸው ወጋ አደረጉኝ። እኔም በንግግራቸው ስለተወጋሁ ሌላ ሳይጨመርብኝ መናገር ጀመርኩ።


 እትዬ ጣይቱ በእርግጥ እርሶ ያሉት  ትክክል ነው። 24 ሰአት የሚተላለፍ የፓርላማ ንግግር ያለበት ራሱን የቻለ ቻናል አለ። ያን የወደደ ያያል። 24 ሰአት የሚተላለፍ የዜና ቻናል አለ። ያን የወደደ ያያል። 24 ሰአት የሚተላለፍ የፊልም ቻናል አለ። ያን የወደደ ያያል። ከመቶ ዓመታት በላይ ያስቆጠረ አንጋፋ ብሔራዊ ድራማ አላቸው። ያን የወደደ ያያል።

ይህ ነው ምርጫ!
ይህ ነው መዝናኛ!

ዘወትር ቅዳሜና እሑድ ማታ የቀኑ ጨዋታ” እያሉ የእግር ኳስ ፍቅር ላለን ሰዎች ፕሪሚየር ሊጉን ያሳዩናል።

ይህ ነው መዝናኛ!
ይህ ነው እይታ!

ይህ ሁሉ እኛ ቤት ቢሆን እንዴት ውብ ነበር? እኔ ኳስ ከልቤ ብወድም አንዳቸውንም የኢትዮጲያ ተጫዋቾችን በቴሌቭዥን መስኮት አይቼያቸው አላውቅም። እዚህ ግን እነ አሌክስ ፈርጉሰን በጋዜጠኞች ይፋጠጣሉ። እነ ሩኒ እየመጡ ካሸነፉ ደረታቸውን እየነፉ ከተሸነፉ ራሳቸውን እያከኩ ይናገራሉ። አሁን ማን ይሙት እኛ ቤት ይህ እንዳይሆን ምን ይከብድ ይሆን? አልኳቸው። እትዬ ጣይቱም እሱስ ምንም አይከብድም ልፋ ያለው በሕልሙ ሸክም ይሸከማል” የሚለው ተረት ብቻ ነው የሚከብደው አሉኝ። እኔም ሳላስበው ድንገት ብሶቴ ከእትዬ ጣይቱ ብሶት ጋር ተደመረ። የቴዲ አፍሮ ዘፈን እንዳይተላለፍ ታገደ ሲባል ሰማሁ። እትዬ ጣይቱ እርሶ ምን ይላሉ? ብዬ ጠየኳቸው። እትዬ ጣይቱ ትንሽ ፍግግ እያሉ የተከለከሉ ነገሮችን የማወቅ ጉጉት የሰው ተፈጥሮ ነውና እገዳው ብዙዎች ጆሮ ሰጥተው እንዲሰሙት ያደርጋል” አሉኝ። እባባላቸው ገረመኝ። እዚህ ጋ የምንነጋገረው ዘፈን ጠምቶን ሳይሆን ስለ ብሮድካስት ነፃነት ነው።

ይህችን ጥሑፍ ጥፌ ልጨርስ ስል እትዬ ጣይቱ ሲባዛ ፕሮግራም ጀምሯል በል ክፈትልኝ አሉ። ኧረ ለመሆኑ አዘጋጆቹ ማባዛት ብቻ ነው እንዴ የተማሩት? መደመር የሚባል ሒሳብም አለኮ። ዝግጅቶችን ብትደምሩልን አንከፋባችሁም። መቀነስም የሂሳብ  ሕግ ነው። ረዘም ረዘም ያሉ ወሬዎችን ብትቀንሱ ከቶ አንከፋም። ኧረ ማካፈልም ሒሳብ ነው። ፕሮግራሞቹን እጥር ምጥን ያለች ዝግጅት ብታደርጉ ማን ይሙት እንዴት ደስ ባለን ነበር። እድለኛ አይደለንምና ማባዛት ብቻ ሆነብን። አንዷን የተቀረፀች ፕሮግራም በመቶ ተባዝቶ መቶ ጊዜ ይቀርባል። የአየር ጊዜኮ ውድ ነው። መቶ ጊዜ በተደጋገሙት ፕሮግራማችሁ ምክንያት ቴሌቭዥኖቻችን የተመጣጠነ ምግብ አጥተው እንዳይከሱ እፈራለሁ! አዬ ሁሉን ቢናገሩ ሆድ ባዶ ይቀራል አሉ እትዬ ጣይቱ ምርር ብለው እንደለመዱት ሆዳቸውን በእጃቸው እየዳሰሱ።


መቼስ በእኔና በእትዬ ጣይቱ የብሶት ንግግር እምዬ ኢቲቪ ሳይቀየሙን አልቀረም። ክፉኛ አዝነውብን ፊታቸውን እንደ ፎጣ አጣጠፉት። በመጨረሻም ኢቲቪ ይህን አባባል ደረደሩ።




“ዕርቅ የፈለገ ንጉሥ ገበሬ ያስታርቀዋል ዕርቅ ያልፈለገን ገበሬ ንጉሥ አያስታርቀውም


ኩርፊያውም ቀረ። እኔም ዕርቅ ያልፈለገውን ገበሬ እንዳልሆን ፈራሁና ስለ ኢቲቪያችን በልቤ ይህን አልኹ።

የልብ ሳይደርስ እድሜ ይደርስ! አሉ እትዬ ጣይቱ።