Saturday 31 March 2012

ለአንዱ ወዳጄ በጠባብዋ የደሀ አልጋዬ ላይ አብረን እንድንተኛ ትንሽ ተጠጋሁለት። እሱ ግን እንዲህ እያለ በሞራሌ ላይ ተሯሯጠ
“የደሀ ግድርድር ሀብታም ይጋብዛል አሉ! ኧረ ተው! ሲጥጥጥ….  አለች እኮ አልጋዋ። ኧረረረ! ልክ እንዳንተ ትንሽ ሲነኳት ትጮኻለች; እኔ የምልህ በለንደን ባልጠፋ አልጋ መፃጉዕ ይተኛባት የምትመስለውን ይህችን አንድፍሬ ምን ልሁን ብለህ ገዛህ?” አለኝ ታላቁ ወዳጄ በጣም እያዘነልኝ። “ማግኘትንም ሆነ ማጣትን አይቻለሁ; ያለኝ ይበቃኛ ማለትን ተምሬያለሁ” የሚለውን ጥቅስ ከግድግዳው ላይ እንዲያነብ በዓይኔ ጋበዝኩት፤ እሱም በዓይኑ ለንባብ አላርጂክ እንደ ሆነ ነገረኝ። በንግግሩ አልጋዬም አዝናለች መሰል  ቋቋቋ…..ሲጥጥጥ….. እያለች ለሊቱን ሙሉ እያለቀሰች አደረች!  ወዳጄ ለምን መሰለህ ይህችን ጠባብ አልጋ የምወዳት? አልኩት። እህሳ? አለኝ። ጠባብ አልጋ የግድ ያስተቃቅፋል!”
ብዬ ማንኮራፋቴን ቀጠልኩ።
*  ይህች ሳምንት ኒቆዲሞስ ትባላለች። በአይሁድ ረበናት ፍራቻ ምክንያት ኒቆዲሞስ ከክርስቶስ ጋር የሚገናኘው በለሊት ነበር፤ ጌታችንም ስለ ጥምቀትና ስለ ነገረ ድህነት አስተምሮታል። ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ሆኖ የክርስቶስን ሥጋ ለመከፈን በቅቷል። ታሪክ እንደነገረኝ ኒቆዲሞስ በመጨረሻ ጳጳስ ሆኗል።
አገልጋይና ንባብ // ብራናውን አምጣልኝ”

      ስትመጣ በጢሮአስ በአክርጳ ዘንድ የተውኩትን በርኖሱንና መጻህፍትን ይልቁንም ብራናውን አምጣልኝ። [2ኛ ጢሞ. 4:13]

የሕክምና ሰዎች ልዩ ልዩ ዓይነት ምግብ የሚመገብ ሰው የተለያዩ ቫይታሚኖች፣ ማዕድኖች እና ገንቢ ነገሮች የማግኘት ዕድሉ ይሰፋል እንደሚሉት ሁሉ ልዩ ልዩ ዓይነት መጻሕፍትን ማንበብም እንደዚሁ ነው፡፡ አንዳንድ መጽሐፍን ለመቅመስ ስንል አንዳንድ መጽሐፍትን ደግሞ ለመመገብ ስንል አንዳንድ መጽሐፍትን ደግሞ ለማጣጣም ስንል እናነባለን፤ እነሆ ንበብ ሰውን ሙሉ ያደርገዋልና።

ቅ/ጳውሎስ ስትመጣ በጢሮአስ በአክርጳ ዘንድ የተውኩትን በርኖሱንና መጻህፍትን ይልቁንም ብራናውን አምጣልኝ ነበር ያለው። እኛ ብንሆን ግን ስትመጣ ቅቤውን አትርሳ! በርበሬውም አይቅር! ኧረ ድርቆሹስ እንደምንም ተቸገርልኝ!! ነበር የምንለው።

ጠበቆች ሕግን በተመለከተ የተጻፉትን መጽሐፍትን በትጋት ያነባሉ፤ የሕክምና ባለሙያዎች ሳይንሳዊ ይዘት ያላቸውን መጽሐፍት ያነባሉ።  እንደዚሁ ሁሉም ባለበት ዘርፍ ሙሉ እውቀት እንዲያገኝ ማንበብ አለበት ማለት ነው።

አንድ ረጅም የባቡር ጉዙ የሚጠብቀው ሰው ራሱን ለንባብ ምቹ በሆነ የባቡሩ ማዕዘን ባለው ወንበር ላይ ይቀመጥና በዚህ ረጅም ጉዞ ለረጅም ጊዜ የሚጠቅመውን ብዙ ዕውቀት ያከማቻል! ባለንበት የአውሮፓዋ ሀገር ሰዎች በጉዟቸው ላይ ማንበብን የሚያዘወትሩት ለዚህ ነውና። ዓለም የምታውቀው በግል ተሽከርካሪው እየተጓዘ መፅሐፍትን የሚያነብ አንድ ታላቅ ኢትዮጲያዊ ነበር። ይህ ሰው ማን ነበር? እሱማ የማንበብን ልምድ ያስተማረን ባኮስ የተባለው ኢትዮጲያዊው ጃንደረባ ነው። ከደገኞቹ ሐዋርያት የነበረው ፊሊጶስም “የምታነበውን ታስተውለዋለህን?” አለው። ወዳጄ የምናነበውን ማስተዋል ታላቅ ነው። ታላቁ መፅሐፍ “አንባቢው ያስተውል!” ይላልና። [ማቴ 24]
እነሆ የግብፅ ፓትርያርክ አቡነ ሺኖዳ የጳፋቸው ብዙ ድንቅ መጽሐፍት አሉ፤ መንፈሳዊ ቃላትና ጥቅማቸው፣ የባሕታዊያን ህይወት…. በዲያቆን ዳንኤል ክብረት ቤተክርስቲያንህን እወቅ… ብናነባቸው እንዴት ታላቅና ጠቃሚ መጽሐፍት ናቸው። እነሆ የአስተሳሰብ አድማሳችንን ለማስፋት ማንበብ አለብን። እናንተ ካነበባችሁት ለእኛ ማካፈልን አትርሱ፤ እስኪ ለዛሬ እኔ ካነበብኩት ታሪክ ላካፍላችሁ፦
ዳግማዊ ምኒልክ (ሕዝቡ በፍቅር እምዬ ይላቸው ነበር) ኅዳር ፳፯ቀን ፲፰፻፹፰ (1888) .. ወላይታ ከጦና ዋና ከተማ ደልቦ ደረሱ፡፡ እዚኽ የመገኘታቸው ምስጢር የወላይታው ንጉሥ ጦና አልገብርም ብሎ በመሸፈቱ እሱን ለማረም ነበር፡፡“…አገር ከጠፋ በኋላ ሲያቀኑት ያሲቸግራል ግብርህን ይዘኽ ግባብለው በሽምግልና ቢሞክሩም መልሱ እምቢታ በመሆኑ አጤ ምኒልክ ዳሞት ተራራ ላይ ያሰፈሩትን ጦራቸውን አዘው በአንድ ጊዜ ወላይታን አስጨነቋት፣ንጉሥ ጦናም ቆስለው ተማረኩ፡፡ የሚገርመው ግን መፍቀሬ ሰብዕ እና የዲፕሎማሲ ሰው የሆኑት አጤ ምኒልክ አይ ወንድሜ እንዲያው በከንቱ ሕዝብ አስጨረስክብለው የንጉሥ ጦና ቁስል እንዲታጠብና እንዲታከም አደረጉ!!! ይህን ሳነብ በጣም ገረመኝ፤ አንድ የመፅሐፍ ቅዱስን ታሪክም ወዲያው ትዝ አለኝ፤ ነብዩ ኤላሳዕ የሶርያን ሠራዊት ካስማረከ በኋላ አብልቶና አጠጥቶ ወደ ሀገራቸው እንደላካቸው! ፪ ነገ ፮            
ታላቁ ሰው ምኒልክ የተማረከው የባላገሩ ከብት እንዲመለስ አድርገው፣ንጉሥ ጦና እስኪያገግሙ ጠብቀው የወላይታን ሕዝብ ሰብስበው“…እንግዲህ ወዲህ የሚያስተዳድርህ ልጄ ወዳጄ ጦና ነውና ተገዛለት፡፡ አውቆ ሳይሆን ሳያውቅ እኔን የበደለ መስሎት ሰው አስጨረሰ እንጂ ከድሮም ከአያቶቻችን ቂም የለንምና መልሼ እሱን ሾሜልሃለው፡፡እንግዲህ ወዲህ ብታምጽ በራስህ ዕወቅ፡፡ ግብሬን አግባ፡፡…”የሚል አዋጅ አስነግረው የወጉዋቸውን ጦናን ሾመው ጥር ፲፩ቀን አዲስ አበባ ገቡ። (አጤ ምኒልክ መጽሐፍ በጳውሎስ ኞኞ)

ወሥበሐት

 ለእግዚአብሔር

ተክለ መድህን

Tuesday 27 March 2012

ነህምያ! ለነገሮች ሁሉ ጸሎትን በማስቀደም እታወቃለሁ፤ በምርኮ ሀገር እያለሁ ሰዎች “የኢየሩሳሌም ቅጥር ፈራርሷል በሮቿም በእሳት ተቃጥለዋል” አሉኝ፤ “ይህን ነገር በሰማሁ ግዜ ተቀምጬ አለቀስኩ ነህምያ [1:4]


“እምዬ ቤተክርስቲያን ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ ባላስታውስሽ ምላሴ ከትናጋዬ ጋር ይጣበቅ"

የለንደን ወጣቶች "ለቤተክርስቲያን ያልሆነ ፓውንድ ይበጣጠስ ብለናል!!"... እውነት እኮ ነው ኪስ ቢገባ አያሞቅ ባንክ ቢገባ አይሞላ! እኛ የስደት ልጆች እናታችን ቤተክርስቲያን ተቸግራ በተደላደለ አልጋ ላይ የሚያርፍ ጎንም ሆነ ሕሊና የለንም!!

እነሆ ባለፈው እሁድ ማታ እስከ 3am ድረስ ስለ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ስናወጣና ስናወርድ አመሸን።

“እምዬ ቤተክርስቲያን ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ ባላስታውስሽ ምላሴ ከትናጋዬ ጋር ይጣበቅ" አልን በእንባ ጭምር!! እንደ ነብዩ ነህምያ አንዳች ስራ ለመስራት በጸሎት ጀመርን።

10 የምንሆን ልጆች የዝቋላ ገዳምን እርዳታ በተመለከተ ምን እናድርግ? አልን። ይህን የመሰለ ውይይት ዘወትር እሁድ ለምደናልና። እንደ ጉድ ሀሳብ አዋጣን፣ እንደ ጉድ ተነጋገርን እንደ ጉድ መፍትሄ መጣ። ሕዝበ ክርስቲያኑን በፌስ ቡክ እና በተለያዩ ዘዴ ሀሳቡን አስረድተን አንዳች ስራ ይሰራ ተባለ። ቀጠሮም ተያዘ። እነሆ በመጪው እሁድ መጋቢት 23 /April 1st/ ከቅዳሴ በኋላ የዝቋላ ገዳምን የእሳት ቃጠሎ የሚያሳዩ ቲሸርቶችንና የተለያዩ ጥቅሶችን በማንገብ ስማ በለው ሕዝቡን እንበል፣ ከ2 ፓውንድ ጀምሮ የተቻለውን ያድርግ ተባለ። ከእኛ ይጀመር ተባለ። ከእኛም ተጀመረ። አንዱ £100 አለ፤ ቀጠለ አንዱ ለቤተክ ያልሆነ! £100 ይሁና አለ። ቀጠለች ሌላዋ £50 አንደኛዋም ተከተለቻት። ያላትን ሰጥታ በጌታ የተመሰገነችው የአንድ ዲናር ባለቤትዋ ሴትም ከእኛ ጋር ነበረችና ከሁላችንም የበለጠ ሰጠች!! እንዲህ እያለ በዚያን ቀን ብቻ * ፓውንድ ተገኘ! ስንት እንዳገኘን በቁጥር መግለጹ ያልተፈለገው ዋናው ልብን መስጠት ነው እንጂ የሒሳብ ክፍለ ግዜ ስላልሆነ ነው።


ገና ሌሎችም የሰ/ት/ቤቱ ተማሪዎች ሲጨመሩ፣ የሕዝበ ክርስቲያኑ በለንደንም በየከተሞቹም ያሉት ሲደማመር ለቤተክርስቲያናችን ጥሩ ፖውንድ ሳይሆን ጥሩ ልብ እናዋጣለን። አሐዱ ተብሎ ሲጀመር እናት ቤተክርስቲያን ልባችንን እንጂ መቼ የእኛን ገንዘብ ፈለገችና? ቤተክርስቲያን ያጣችው ገንዘብ ሳይሆን ቅ/ጳውሎስን የመሰለ ሁነኛ ልብ ነው። ወዳጄ ሆይ ማወጣት ፈልገህ ባይሆንልህ ልብህን አዋጣ! አዎ ልብህን ለቤተክርስቲያን ስጥና ያንኑ አዋጣ።

ወጣት የነብር ጣት ሆይ ጊዜው አሁን ነው ። እስኪ በአውሮፓም ፣ በአረብ ሀገር ፣ በአለም ሁሉ ያለን የቤተክርስቲያን ልጆች ይህን የመሰለ ህብረት ፍጠሩና አንዳች ስራን እንስራ። በያላችሁበት የሰ/ት/ቤቱን ወጣት አስተባብሩና ስሩ፤ ብርቱ ጉዳይ አለብንና ጊዜው የስራ ነውና ወዳጄ ሆይ ልብህ አይተኛ። የቤተክርስቲያን ድምጽን ስትሰማ ተፈጥሮ ነውና ዓይንህ ቢዘጋ ልብህ ግን አይተኛ! ቤተክርስቲያንን የሚያቃጥል እሳት የእኛንም ልብ ያቃጥላል! የቀደሙት አባቶቻችን እሳት ላይ ቆመው የጠበቁልንን ቤተክርስቲያን እኛ ይህን እሳት ማጥፋት ካቃተን የእኛ መኖር ምኑ ላይ ነው? ለቤተክርስቲያን ድምጽ ዲዳው ይናገራል መስማት የተሳነውም ይሰማልና እስኪ ህዝቡን አስተባቡሩ እስኪ በስደትም ሆነ በሀገር ያለን ሁላችንም እንነሳና እያንዳንዳችን ቢያንስ 2 ችግኝ እንትከል፤ አንዱ ቢደርቅ አንዱ ይጸድቃልና!!

እነሆ ገዳሙን መርዳት የምትፈልጉ ምእመናን ከዲ/ዳንኤል ክብረት ብሎግ ኮፒ እንደተደረገው የገዳሙ የባንክ አድራሻ የሚከተለው ነው፡፡
ለዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
ቢሾፍቱ ቅርንጫፍ
የባንክ የቁጠባ ሂሳብ ቁጥር 19789
በአካውንቱ የላካችሁ ምእመናን በኢሜይል አድራሻ dkibret@gmail.com መላካችሁን ብትገልጡልን ለገዳሙ መልእክቱን ለማቀበል ይረዳናል



“እምዬ ቤተክርስቲያኔ ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ
ባላስታውስሽ ምላሴ ከትናጋዬ ጋር ይጣበቅ"

ለቤተክርስቲያናችን ፍፁም ሰላም ክብርና ሞገስ ይስጥልን አሜን።

እኛ ባርያዎቹ እንነሳለን የሰማይ አምላክም ያከናውንልናል ነህምያ 2:20

ከለንደን ቅ/ሥላሴ ቤተክ ሰ/ት/ቤት