Monday 28 November 2011


“ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ”

v እስራኤላዊያን ኀዘናቸውን የሚገልፁበት ለየት ያለ ባህላዊ አገላለጽ አላቸው፤ “ሲያዝኑ ልብሳቸውን ይቀዳሉ!
ለምሳሌ የዳዊት ልጅ አምኖን በገዛ እህቱ በትዕማር ላይ የማይገባ ድርጊት ፈፀመ፤ አምኖን ትዕማርን በፈቃደ ሥጋ አስነወራት። ትዕማርም ልብሷን ቀደደች፤ ታላቅ ሃዘኗንም ገለፀች [2ኛ.ሳሙ13:1]

እስራኤላዊያን ደናግል ሴቶች የሚለብሱት እጅግ ያማረ ቀሚስ አላቸው፤ ድንግል አይደለንም ሲሉ ይህን ልብሳቸውን ይቀዳሉ፤ የዛሬ እህቶቻችን በሀገር ቤትም ሆነ በውጭው አለም ልብሳቸውን ሲቀዱ ምን ማለታቸው እንደሆነ ሊረዱ ይገባቸዋል ማለት ነው!
v ትዕማር ልብሷን ቀዳ ሃዘኗን እንደገለፀችው ሁሉ
ሴኬም የተባለው ሰው የያዕቆብ ልጅ የነበረችውን ዲናን ባስነወራት ግዜ ልብሷን ቀዳ ታላቅ ሃዘኗን ገልፃለች [ዘፍ. 34:1]

እነሆ እስራኤላዊያን ሃዘናቸውን የሚገልፁት ልብሳቸውን በመቅደድ እንዲህ ባለ መልኩ ነው፤ በዚህ ምክንያት ነበር እግዚአብሔር በነብዩ ኢዩኤል አድሮ እንዲህ ያለው፦


“ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ”
በፆምና በፀሎት በፍፁም ልባችሁ ወደ እኔ ተመለሱ [ኢዩኤል2:12]   
    
v  የነብያት ፆም፦  እስራኤላዊያን በአንድ ወቅት ለምን
ጾማችን በእግዚአብሔር አይሰማም? ብለው ይጠይቁ ነበር፤ በውኑ ብዙ ግዜ ጾማችን የማይሰማው ለምን ይሆን? ለዚህ የእስራኤላዊያን ጥያቄ ነብዩ ኢሳይያስ ድምፁን ከፍ አድርጎ  ለእስራኤላዊያን  መለሰላቸው፤ እነሆ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦

በውኑ እኔ የመረጥኩት ፆም ይህ ነውን? ፆማችሁ በጥልና በክርክር የተከበበች ናት፤ የልባችሁን ሁሉ ትፈጽማላችሁ፤
በውኑ እኔ የመረጥኩት ፆም ይህ ነውን? ኢሳ 58:5

ዛሬም እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ እኛን ይጠይቀናል “በውኑ እኔ የመረጥኩት ጾም ይህ ነውን”? እግዚአብሔር የመረጠው ጾም ምን አይነት ጾም ይሆን? መልሱን በወንጌል ላይ እንዲህ እናገኘዋለን፦  ስትጾሙ እንደግብዞች አትጠውልጉ ፊታችሁን በፍቅር ቅባት ተቀብታችሁ የምትጾሟት ጾም ታላቅ ዋጋ አላት [ማቴ. 6: 16]

ልበ አምክ ዳዊት ከመጾሙና ለመዘመር በገናውን ከመደርደሩ በፊት እንዲህ አለ፦ አቤቱ ንፁህ ልብን ፍጠርልኝ// ልበ ንጹኃ ፍጥር ሊተ እግዚኦ [መዝ. 50: 10] ዳዊት ንጹህ ልብን ፍጠርልኝ ብሎ ከለመነ በኋላ በገናውን እየደረደረ ዘመረ ጾመ ፀለየ ፤ ጾምና ዝማሬውም በእግዚአብሔር ተሰማች! እኛም ለመዝሙር በገና ከመደርደራችን፤  ከመጸለያችንና ከመጾማችን በፊት አቤቱ ንፁህ ልብን ፍጠርልኝ ማለት እንዳለብን ልበ አምላክ ዳዊት አስተማረን።

v  ስለ ጾም በወንጌል ላይ እንዲህ ተጽፏል ይህ ጋኔን ያለ ጾምና ፀሎት
አይወጣም” // ዝንቱ ዘመድ እይወጽዕ ዘእንበለ ጾም ወበ ፀሎት [ማቴ. 17: 21]
ጾም አጋንንትን እንዃን የማስወጣት ታላቅ ሃይል አለው!!!  ነገር ግን የመናፍቃኑን መፅሐፋ ቅዱስ ስንመለከት ይህን ቁጥር ዘለውታል! ጾም አጋንንትን ለማውጣት ሃይል እንዳለው ስለሚናገር የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 17 ቁጥር 21 የሚለው እንዳለ ተዘሏል!

እኛ ግን ከስራችን በፊት ሁሉ መጾም ይገባናል፤ ሐዋርያቱ ከአገልግሎታቸው በፊት ጾሙ ጌታም ተዓምራት ከማድረጉ በፊት እኛን ሊስተምረን ጾመ እነ ዳዊት ንጉሥ ሆነው ሳለ ጾሙ፤ ነብያቱ ሁሉ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሰው መሆን በተስፋ እየተጠባበቁ    ጾሙ! 

ጾምሰ እማ ለፀሎት ወእህታ ለአርምሞ ወነቃየ ለአንብዕ // ጾም የጸሎት እናት የትዕግሥት እህት የንስሃ እንባ ምንጭ ናት!!!







እንደነ ዳዊት በንጹህ ልብ የምትጾም ጾም ዋጋዋ ታላቅ ናት፤ ለዚህ ነው ዲያቆኑ በቅዳሴ እንዲህ የሚለው፦ ሰው በልቦናው ቂምን እና በቀልን ማንም በማንም ላይ ቢሆን አይያዝ // ትዕዛዝ አበዊነ  ሐዋርያት እያንብር ብዕሲ ውስጠ ልቡ ቂመ ወበቀለ በቅንአተ ላዕለ ቢፁ ወኢላዕለ መኑሂ።

የተጣላን ታርቀን የበደልን ይቅርታ ጠይቀን ከሃጢአት ሁሉ ርቀን ዋጋ ያላት ደስ የምታሰኝ፤ የእግዚአብሔርን ፀጋ ፤ ምህረቱን፤ ቸርነት ደግነቱን
የምንቀምስበት ጾም ትሁንልን ፤አሜን። ወሥበሐት ለእግዚአብሔር
[ተክለ መድህን]



“ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ”

በፆምና በፀሎት በፍፁም ልባችሁ ወደ እኔ ተመለሱ

[ኢዩኤል2:12]

-//-
 

1 comment:

Anonymous said...
This comment has been removed by a blog administrator.