Saturday 31 December 2011

እንተዋወቅ ስም፦ ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስ እባላለሁ

እንተዋወቅ

ስም፦ ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስ እባላለሁ
ሀገር፦ መንግስተ ሰማያት
ዜግነት ፦ ክርስቲያን
ስራ፦ እግዚአብሔርን አመልካለሁ

+++ ይህ ስም ክቡር ነው! “ብርሐነ ዓለም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ”

የመጀመሪያ ስሙ ሳውል የተባለው ይህ ምርጥ እቃ “ሰርግዮስ ጳውሎስ” ለተባለ ሃገረ ገዢ ብርኀን ወንጌልን ያስተምረው ነበር፤ ነገር ግን የሙሴን በትር እንደተቃወሙት ሁለቱ ጠንቋዮች /ኢያኔስና ኢያንበሬስ/ ሳውልንም የሚቃወም “ኤልማስ” የተባለ ጠንቋይ ነበር፤

ይህ ኤልማስ የተባለው ጠንቋይ ሳውል ወንጌልን ለሃገረ ገዢው /“ለሰርግዮስ ጳውሎስ”/ እንዳይሰብክለት ትልቅ እንቅፋት ሆነበት፤ ሳውልም ለጠንቋዩ ኤልማስ “አንተ ጨለማ ሆነህ በእውነት ብርኀን ወንጌልን ተቃውመሃልና እነሆ በጨለማ ትመታለህ” አለው። ጠንቋዩ ኤልማስም ወዲያውኑ ጨለማ ወረሰውና ዓይኑ ተያዘ፤ ሃገረ ገዢው ሰርግዮስ ጳውሎስም የኤልማስ ዓይነ ሥጋ ሲጨልም፣ የራሱም ዓይነ ልቡና ሲበራ አየና ለሳውል “ስምህ ሳውል አይሁን "ጳውሎስ" ማለት ብርኀን ማለት ነውና አንተም ዓይነ ልቡናዬን በወንጌል ብርኀን አብርተሃልና ስምህ //ጳውሎስ// ይባል ብሎ የራሱን ስም ሰጠው። [ሐዋ. 13: 7]

ጳውሎስ! ይህ ስም ክቡር ነው! እነሆ “ጳውሎስ” ማለት “ብርኀን” ማለት ነውና “ብርኀነ ዓለም ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስ” ብለን ጠራነው። ስሙ በራሱ ብርኀን ማለት ሲሆን ከስሙ አስቀድመን "ብርኀነ ዓለም" ብለን እኛም እንደ ሃገረ ገዢው እንደ ሰርግዮስ ጳውሎስ ስንጠራው የፃፋቸው መልዕክቶችም ብርኀን ሆነው ይነበባሉ!

ለህፃናት የምናወጣላቸውን ስሞች እንዲህ ትርጉም ሲኖራቸው መልካም ነው፤ ይህን በተመለከተ በአንድ ወቅት ያጋጠመኝን እውነተኛ ታሪክ ልንገራችሁ፤

ባለሁበት በለንደን ከተማ አንዲት እናት ለሴት ልጇ ደስ ይላል ያለችውን ስም አወጣችላት፤ ምን የሚል ስም መሰላችሁ? የልጅቷ ሥም “ሜልኮል” የሚል ነበር። ስሙን ስንሰማ ገረመንና እንዴት ልጅሽን “ሜልኮል” ብለሽ ጠራሻት? አልናት። እናትየውም የዳዊት ሚስት ናት ሲባል ስለሰማሁና ስሙን ስሰማ ስለወደድኩት “ሜልኮል” ብዬ ጠራኋት አለችን። “ሜልኮል” እኮ ልጅ እንዳትወልድ ማህፀንዋን እግዚአብሔር የዘጋባት ሴት ናት ብለን እነሆ “ሜልኮል” የተባለችው ቆንጅዬ ልጅ ቤተልሔም የሚል አዲስ ስም ወጣላት።

+ ዕራቁታቸውን የሮጡት 7ቱ ሰዎች፦
ወይወስዱ እምፅንፈ ልብሱ ወያነብሩ ዲበድውያን ወየሃይው ወአጋንንት እኩያን ይወፅኡ እንዲል የቅ/ጴጥሮስ ጥላ በሽተኞችን ሲፈውስ የቅ/ጳውሎስ የልብሱ ቁጨት ደግሞ አጋንንትን አወጣ! [ሐዋ. 5 ፤ 19:12]

ቅ/ጳውሎስ አጋንንትን ሲያወጣ ብዙ ሰዎች ተዓምሩን አዩ፤ የካህናቱ አለቃ የአስቄዋ 7 ልጆች ግን “ጳውሎስ በሚሰብከው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ውጡ” እያሉ አጋንንትን ለማስወጣት ሞከሩ። አጋንንትም ኢየሱስን ዐውቀዋለሁ ጳውሎስንም ዐውቀዋለሁ እናንተ ግን እነማን ናችሁ? ብለው ዘለው ያዙዋቸው! በሰዎቹም ላይ እጅግ ስለበረቱባቸው ቤቱን ጥለው ዕራቁታቸውን ሮጡ ይለናል!! [የሐዋ. 19:12]

+++ ቤተክርስቲያንና ቅ/ጳውሎስ፦
ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስ ለቤተክርስቲያን እጅግ ይቀና የነበረ ሐዋርያ ነው። ቅ/ጳውሎስና ቤተክርስቲያን የአንድ ዕርግብ ሁለት ክንፍ እንደማለት ናቸው!! ሁለቱም አይለያዩምና; በቀዝቃዛ እስር ቤት እያለ ቅ/ጳውሎስ ያስብ የነበረው ለቤታክርስቲያን ነበር። አብዛኛውን መልዕክታቱንም የፃፈው ከምድር በታች ባለች ቀዛቃዛ እስር ቤት ውስጥ ነበር። 2ኛው የጢሞቴዎስ መልዕክት የተፃፈውም በቀዛቃዛዋ እስር ቤት ነበር!!!

ቅዱስ ጳውሎስ መልእክታቱን የጻፈባቸው ቀዝቃዛ እስር ቤት ይህን ይመስላል;
ልእ እንደ ለንደን ባቡር መሄጃ / /under ground/ ሲሆን ካታኮምቦ /ግበበ ምድር/ ይባላል።

+++ ሐዋርያዊ ስራዎቹ፦ ይህ ታላቅ ሐዋርያ ከሐዋርያት ሁሉ ብዙ መንገድ በእግሩና በባህር በመጓዝ የደከመና በጉዞው ህይወቱን ለአደጋ ያጋለጠ ሲሆን ለአህዛብ ወንጌልን ለመስበክ በመመረጡ 16 መልዕክታትን ጽፋል፤ ሁለቱ ጠፍተው በመጽሐፍ ቅዱስ ያለው 14ቱ መልዕክታቱ ናቸው።

+++ ዕውቀትን ከትህትና ጋር ደርቦ የያዘ ነበር፦
በእየሩሳሌም በሚገኘው በታላቁ የአይሁድ ት/ቤት ከሊቁ ከገማልያል እግር ስር ቁጭ ብሎ ብሉይን የተማረና አዲስ ኪዳንን አበጥሮ የሚያቃት ቢሆንም በእውቀቱ አልተመካም፤ እኔ ጭንጋፍ ነኝ እስከማለትም ደርሶ ነበር። 1ቆሮ. 15:8

+++ ሥራ ወዳድ ነበር፦
ሌት ተቀን በወንጌል ቢደክምም ለምዕመናን እንዳይከብዳቸው ድንኳን እየሰፋ እራሱን ይችል ነበር!!!

+++ እጅግ ትዕግስተኛ ነበር፦
ብዙ ግዜ ቢታሰርም በረሃብ ቢደክምም መልዕክቱን በትዕግስት ሆኖ በደስታ ይጽፍ ነበር፤ በጌታ ደስ ይበላቹ ደግሜ እላለሁ ደስ ይበላቹ እያለ በመልዕክቱ ያጽናና ነበር።

+++ ተግባቢ ነበር፦
ቅ/ጳውሎስ ሰውን እንዴት መቅረብ እንዳለበት ያውቅ ነበር። ከተራ ሰዎች እስከ ነገስታት በፍቅር እየሳበ ክርስቲያን አድርጓል። በመልዕክቱ መጨረሻ የቤተክርስቲያንን ልጆች ስም እየጠራ ሰላምታ ማቅረብ የዘወትር ተግባሩ ነበር።

+++ ጥበበኛ ነበር፦
የቤተክርስቲያን አበው ቅ/ጳውሎስን መዶሻ ይሉታል። መዶሻ ማዕድናቱን ቀጥቅጦ አንድ እንደሚያደርግ ሐዋርያውም አህዛብንና ሕዝብን/እስራኤል ዘሥጋን/ አንድ ስላደረገ ነው። በጉዞው ቲቶንና በርናባስን አስከትሎ ነበር; ቲቶ ግሪካዊ አህዛብ ሲሆን በርናባስ ደግሞ አይሁዳዊ ነበር።

+++ በመጀመሪያ የቤተክርስቲያን አሳዳጅ ነበር፦
ቅ/ጳውሎስ በ32 አመቱ ክርስቲያንን ለማጥፋት ከሊቀ ካህናቱ ቀርቦ የፍቃድ ደብዳቤ ከተቀበለ በሗላ የሶርያ ዋና ከተማ ወደሆነችው ወደ ደማስቆ ሊደርስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ሞላውና “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ" የሚል ድምጽ የሰማው። በመቀጠልም ለሐዋርያነት ተጠራ።

+++ ታላቅ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፦ በዘመኑ የነበረው ጨካኙ ንጉስ ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት; የሮም ሕዝብ በክርስቲያን ላይ አሳበቡ፤ በዚህም ክርስቲያኖች ሰማዕት መሆን ግድ ሆነባቸው። ቅ/ጳውሎስም ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ እስር ቤት ታስሮ ከቆየ በሗላ በ74 ዓመቱ በሮማ ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሠይፎ ሐምሌ 5 67 ዓ.ም በሰማዕትነት ዐረፈ።

ብርሐነ አለም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ
ሰማእትነትን እንደተቀበለ
“ሩጫዬን ፈጽሜያለሁ ሐይማኖቴን ጠብቄያለሁ
የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል” 2ኛ ጢሞቴዎስ 3:4

የእግዚአብሔርን ቃል የተናገራችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ; የእምነታቸውንም ፍሬ እየተመለከታቹ በህይወታቸው ምሰሏቸው ዕብራዊያን 13:7። ታላቁ ሐዋርያ ቅ/ጳውሎስ እንዲህ እንዳለው መላው ህይወቱ ትምህርት ትሁነን፤ አሜን። -//-

እንተዋወቅ

ስም፦ ሐዋርያው ቅ/ጴጥሮስ እባላለሁ
ሀገር፦ መንግስተ ሰማያት
ዜግነት ፦ ክርስቲያን
ስራ፦ እግዚአብሔርን አመልካለሁ

+++ ቅ/ጴጥሮስ ለሐዋርያነት ከመጠራቱ በፊት፦ ቅ/ጴጥሮስ የመጀመሪያው ስሙ ስምኦን ሲሆን የተወለደውም በጥብርያዶስ ባህር ዳር በምትገኘው በቤተሳይዳ ነበር። የአባቱ ስም ዮና ይባላል፤ ከአምስት አመቱ ጀምሮ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር ሆኖ በታላቋ ጥብርያዶስ ባህር መረባቸውን ዘርግተው አሳ ማጥመድ ጀመሩ። ይሄኔ ነበር ጌታ ወደ ወንድማማቾቹ ጠጋ ብሎ ቅ/ ጴጥሮስን ተከተለኝ ያለው። ታላቁ ሐዋርያ ቅ/ጴጥሮስ ለሐዋርያነት ሲጠራ ዕድሜው 55 ዓመት ነበር።

ቅ/ጴጥሮስና ቅ/እንድርያስ አሳ እያጠመዱ // ለሐዋርያነት ሲጠሩ

+++ ድንቅ ሐብተ ፈውስ በቅ/ጴጥሮስ፦ እግዚአብሔር የፀጋ ስጦታ ለቅዱሳኑ ሰቷቸው ድንቅ ተዓምራትን ይሰሩ ነበር። ቅ/ጴጥሮስ ጥላው ድውያንን ሲፈውስ ቅ/ጳውሎስ ደግሞ የልብሱ ቁጨት አጋንንትን አወጣ የሐዋ.5:15 ፤ 19:12

+++ ንስሐ ቅ/ጴጥሮስ፦ በቤተክርስቲያናችን በንስሐ ከሚታወቁት መካከል ቅ/ጴጥሮስና ልበ አምላክ ዳዊት ቀደምት ናቸው ፤ ሁለቱም "ንስሐ አበው" በመባል ይታወቃሉ። ቅ/ጴጥሮስ ምንም እንኳን በፍራቻ ጌታውን ቢክድም ከካህናቱ ግቢ ወቶ ሥቅስቅ ብሎ አልቅሷል። የቅ/ጴጥሮስ ዕንባ ልክ እንደ ጅረት ወንዝ ያለ ታላቅ የንስሃ ዕንባ ነበር። በንስሃ የታወቀው ክቡር ዳዊትም እንዲህ አለ፦

“ለሊቱን ሙሉ አልጋዬን አጥባለሁ፤ መኝታዬንም በለቅሶዬ አርሳለሁ
አቤቱ በሂሶጵ እርጨኝ እነጻማለሁ” መዝ 6:6 እና መዝ 50

ንስሃ ዳዊት ወጴጥሮስን የተቀበለ የኛንም የንስሃ ልቅሶ ይቀበለን፤ አሜን። ቅ/ጴጥሮስ ጌታን 3 ግዜ ክዶት ነበርና ጌታም 3 ግዜ ትወደኛለህን ብሎ ጠየቀውና ክርስቲያኖችን በመንፈሳዊ ደረጃቸው ከፍሎ ግልገሎቼን ጠብቅ; ጠቦቶቼን ጠብቅ; በጎቼን ጠብቅ ብሎት 3 ግዜ ደጋግሞ አዘዘው፤ ንስሃውንም ተቀበለ። በጣም የሚደንቀው ቅ/ጴጥሮስ መጀመሪያ በተጠራባት በጥብርያዶስ ባህር ጌታ ዳግም ተገልጾ እንዴት ትክደኛለህ ብሎ አዳች አለማስታወሱ ነው ፤ እኛም በንስሃ ስንመለስ "ትላንት ምን ነበርክ? ትላንት ምን ነበር ስራሽ"? ብሎ አንዳንች ሳያነሳ እንዲሁ እጆቹን ዘርግቶ የሚቀበል ሃዳጌ በቀል / በቀልን የሚተው/ አምላክ ክብርና ምሥጋና አምልኮትና ውዳሴ ለእግዚአብሔር ይሁን፤ አሜን።

+++ የቅ/ጴጥሮስ ድንቅ አማናዊ አባባል በቂሣሪያ፦ በእነ ቅዱስ ጴጥሮስ ዘመን የነበሩ ሰዎች ጌታን ግማሹ ከነብያት አንዱ ነው ሲል ሌላው ኤልያስ ነው ደግሞም ሙሴ ነው ይሉ ነበር ፤ እናም ጌታ ሐዋርያቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል” ብሎ ጠቃቸው; ቅ/ጴጥሮስም እንዲህ አለ፦ አንተ ውእቱ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው / አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ/ ብሎ ለአይሁድ ሊቃውንት የተሰወረውን ምስጢረ ተዋህዶ ገልጦ በመመስከሩ ጌታችን “አንተ ጴጥሮስ ነህ” ብሎታል ፤ ጴጥሮስ በላቲን ቋንቋ ፔትራ ሲባል ዐለት ማለት ነው። በአራማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል።

+++ የቅ/ጴጥሮስ ድንቅ አማናዊ አባባል በቅፍርናሆም፦ በቅፍርናሆም ጌታችን ምሥጢረ ቁርባን ሲያስተምር አይሁድ ስላልገባቸው ወደሗላ አፈገፈጉ። ብዙ ግዜ ጌታ በምሳሌ ያስተምርና ካልገባቸው ምሳሌውን ይተረጉምላቸው ነበር ፤ ለምሳሌ ከአይሁድ እርሾ ተጠበቁ ሲላቸው ሐዋርያቱ ዳቦ ስላልያዙ የተነገራቸው መስሏቸው ነበር; ጌታም ተዐቀቡኬ እም ሐሳውያን ነቢያት ፤ /ከሐሰተኞች መምህራን ተጠበቁ / ብሎ አስረዳቸው። ይህን ያመጣንበት ምክንያት አለ፤ ይህም ጌታ ስለ ምሥጢረ ቁርባን ሲያስተምር አይሁድ እንዴት ሥጋዬን ብሉ ይለናል? እንዴትስ ለእኛ ለሁላችን ይበቃናል? ብለው አጉረምርመው ነበር። ይህ ግን ምሳሌ ሳይሆን አማናዊ ሚስጢር ነውና ከላይ እንዳየነው እንደ እርሾው ምሳሌ አልተተረጎመላቸውም፤ ወርቁም ሰሙም ይህ ነውና “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” ዩሐንስ 6:54።

ልብ በል ከርእሴ አልወጣሁም; ቅ/ጴጥሮስ ያለውን ለማምጣት ነው፤ አይሁድ ወደኋላ ሲመለሱ ጌታችን ሐዋርያቱን “እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላቹ?” ብሎ ጠየቃቸው ፤ በዚህን ግዜ ቅ/ ጴጥሮስ “ጌታ ሆይ ወደማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን” በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመሰከረው እርሱ ነው። ዩሐ. 6:66። ቅ/ ጴጥሮስ በቂሳሪያ እንደመሰከረ በቅፍርናሆም ደግሞ ሐዋርያቱን ሁሉ ወክሎ የመሰከረ የሐዋርያት አለቃ ነው።

የቅ/ጴጥሮስ ሰማዕትነት፦
በሰማዕትነት ያለፈው በሮሜ ከተማ ሲሆን በዛች ከተማ ለ25 ዓመታት እንዳስተማረ የሮማ ሰዎች ይናገራሉ፤ ከጌታ ጋር 3 ዓመት ከ3 ወር; ዙሮ በማስተማር ደግሞ ለ27 ዓመታት ቆይቷል። የዘመኑ ጨካኝ ንጉስ ኔሮ ቅ/ጳውሎስን እንዲሰየፍ በማድረጉ ክርስቲያኖች ቅ/ጴጥሮስን ባይሆን አንተ ትረፍልን ብለውት በከተማዋ ግንብ በገመድ አስረው በቅርጫት በማውረድ ቅጽረ ሮማን ለቆ እንዲወጣ አደረጉት ፤ በሸመገለ ጉልበቱ እያዘገመ ሲጓዝ ጌታን በመንገድ ላይ አገኘው; ቅ/ጴጥሮስም ጌታዬ ወዴት እየተጓዝህ ነው? አለው ጌታም
“ዳግም በሮማ ልሰቀል” አለው። ቅ/ጴጥሮስም አዘነና ወደ ሮማ ተመልሶ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም ብሎ ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ!!

ዳግም በሮማ ልሰቀል ነው // እንደ ጌታዬ ሳይሆን ቁልቁል ስቀሉኝ

“እስመ ፀላኢክሙ ጋንኤን ይህጥር ከመ አንበሳ ዘይሃስስ ዘይውሃጥ"
"ንቁ ጠላታቹ ዲያቢሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሳ አንበሳ በዙሪያቹ ይዞራል”
1ኛ ጴጥሮስ 5:8 -//-

እንተዋወቅ

ስም፦ ሐዋርያው ቅ/ማቴዎስ እባላለሁ
ሀገር፦ መንግስተ ሰማያት
ዘር ፦ ደግ ክርስቲያን
ስራ፦ እግዚአብሔርን አመልካለሁ

ከሐዋርያት ሁሉ በሀገራችን ያስተማረው ሐዋርያው ማቴዎስ ሲሆን ከነብያት በሀገራችን ለ2 አመት በእግሩ የተጓዘው ደግሞ ነብዩ ኢሳያስ ነው። ኢሳ. ምዕ 20:3

Ethiopia stretching out her hands onto God
ኢትዮጲያ ታበጽህ እዴሃ ሐበ እግዚአብሔር
መዝ 67:31

+++ ማቴዎስ ለሐዋርያነት ከመጠራቱ በፊት ፦ የመጀመሪያው ስሙ ሌዊ ሲሆን ማቴዎስ የሚለውን ስም ያወጣለት ጌታ ነው ፤ ትርጉሙም የተመረጠ ማለት ነው። ማቴዎስ የቀድሞ ስራው ቀራጭነት /tax collector/ ሲሆን ይሰራበት የነበረበትም ቦታ በገሊላ ባህር በምትገኘው በደማቋ በቅፍርናሆም ከተማ ነበር። በዚህች ከተማ ሱቅ ከፍቶ ነጋዴዎችን ቀረጥ ያስከፍል ነበር። ጌታችንም ወደ ማቴዎስ ጠጋ ብሎ ተከተለኝ አለው፤ ማቴዎስም ሁሉን ትቶ ተከተለው።

ማቴዎስ ቀረጥ ከሚሰበስብበት ቦታ ሲጠራ

ቅ/ማቶዎስ የሚያገኘው አልበቃ ብሎት ከአቅም በላይ ገንዘብ እየቀረጠ ነጋዴዎችን እንዳላስመረረ ድኾችን በነጻ የሚያበላ ድውያንን በነጻ የሚፈውስ ሲያገኝ ተገርሞ ስራውን ርግፍ አድርጎ ተከተለው። አበው ቅ/ማቴዎስን የቁም ተዝካሩን አውጥቶ ጌታን የተከተለ ሐዋርያ ነው ይሉታል; ምክንያቱም ለሐዋርያነት ሲጠራ በቤቱ ድግስ ደግሶ ነዳያንን ጠርቶ ጌታን ጋብዞታልና ነው።

+++ ሐዋርያው ይኖርባት የነበረችው ከተማ በጥቂቱ፦ ማቴዎስ ይኖር የነበረው በቅፍርናሆም ከተማ ሲሆን "ቅፍርናሆም" ማለት የናሆም ከተማ ማለት ነው፤ በዚህች ከተማ ጌታ በመዋዕለ ሥጋዌው ከ 11 በላይ ታላላቅ ተዓምራትን አድርጓል። በማቴዎስ የትውልድ ከተማ; በቅፍርናሆም በሚገኘው በጥብርያዶስ ባህር አሳን አበርክቶ አበላቸው ፣ በባህር ላይ ተረማመደ ፣ ጎባጣ ተቃና ለምጽ ነጻ እነ በጥለሚዎስ እውራኑ ሁሉ ብርሐናቸውን አገኙ። ወንጌል ዘማቴዎስ ምዕ 20:34 ፤ ማር 10:46። ከሚበላው አሳን አበርክቶ አበላቸው ከሚታየው ህሙማንን ፈወሰ፤ ነገር ግን የቅፍርናሆም ነዋሪዋች በእምነታቸው እጅግ ቀዝቃዛ ነበሩ፤ ጌታም በዚህች ከተማ ብዙ ተዓምራትን ሊሰራ አልፈቀደም፤ ጌታ በወንጌል ላይ በእምነት ምክንያት ሁለት ግዜ ተደነቀ ተብሎ ተጽፋል፦

አንደኛው በቅፍርናሆም ነዋሪዎች በእምነታቸው ጎዶሎነት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በቅፍርናሆም ከተማ ይኖር በነበረውና “ቃል ብቻ ተናገር ልጄም ይፈወሳል” ባለው በሮማዊው ወታደር በእምነቱ ጽናት ነበር። በማቴዎስ ወንጌል ልጁ ታሞ ሲል በሉቃስ ወንጌል ደግሞ አገልጋዩ ይለዋል; ይህም ወንጌላቱ ተሳስተው ሳይሆን እንደ ልጁ የሚወደው አገልጋዩ ነው ይላሉ አበው። ወንጌል ዘምቴዎስ ምዕ 8:5 ፤ ሉቃስ 7:1።

ወደ ቀደመው ስንመለስ እምነት ወሳኝ ነውና ጌታም ሮማዊውን ወታደር በእምነቱ አድንቆታል; ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስም “እምነትና በጎ ሕሊና ይኑርህ” እንዳለ መልዕክተ ሐዋርያው ቅ/ጳውሎስ ሀበ ጢሞቴዎስ 1ኛ ጢሞ. ምዕ 1:19። እኛንም በእምነት በዝማሬው ቀዝቃዛ ከመሆን ይጠብቀን፤ አሜን።

ስለ እምነት ዕብራዊያን ምዕ 11 ላይ ብዙ ተጽፋልና ልናነብ እንችላለን። ወደ ቀደመው ሃሳባችን ስንመለስ ሐዋርያው ማቴዎስ የተጠራው እምነተ ጎዶሎ ከሆነችው ከቅፍርናሆም ከተማ ነበር። የእግዚአብሔር አጠራር ልዩ ልዩ ነውና; አብርሐምን ከጣዖት አምላኪ ቤተሰብ የጠራ እነ መጥምቁን ዩሐንስን ደግሞ ከማህጸን ጀምሮ መረጣቸው፤ ቅ/ ጳውሎስን ከደማስቆ የጠራ ማቴዎስንም ከቅፍርናሆም ጠራ። እኛስ ከየት ነበር የተጠራነው? እንደ ናትናኤል ከበለስ ዛፍ ስር ወይስ እንደነ ቅ/ጴጥሮስ በአለም አሳን ለማጥመድ ስንደክም? አዎ ከተለያየ ቦታ ተጠራን፤ የጠራን ከእናታችን ከቅድስት ቤተክርስቲያን አንድ ያደረገን ያለየን ልዑል እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን ፤ አሜን

“ከቤተመንግስቴ ከአእላፈት ቀን ይልቅ በቤትህ ልጣል ወደድኩ”
መዝ 83(84) ቁጥር 10

“ወንጌል ዘማቴዎስ”

+++ የማቴዎስ ወንጌል ከማርቆስ በኋላ በሁለተኛነት ተጽፎ እያለ የመጀመሪያውን ተርታ ያገኘው ለብሉይና ለሐዲስ ኪዳን ድልድይ ስለሆነና የብሉይ ኪዳን ምሳሌ በሐዲስ ኪዳን መፈጸሙን ስለሚያሳይ ነው።

+++ ሐዋርያው ወንጌሉን የፃፈው ለአይሁድ በመሆኑ ከ150 በላይ የብሉይ ኪዳንን ጥቅሶች አቅርቧል፤ በዚህም የብሉይ ኪዳንን ጥቅስ አብዝቶ በመጥቀስ ከሌሎች ወንጌሎች ይበልጣል። ከ 1068 ቁጥሮቹ መካከል 644ቱ የጌታ ትምህርቶች ናቸው። ይህም ከወንጌሉ 60% ማለት ነው።

+++ የማቴዎስ ወንጌል በመናፍቃኑ ዓይን፦ ማቴ 17:14፤
አንድ ሰው በጣም የሚወደው ልጁን አጋንንት ያሰቃይበት ነበር፤ አንዴ እሣት ላይ ደግሞም ወደ ባሕር እየወሰደው በጣም አሰቃየው; ይህ አጋንንት ከልጅነቱ ጀምሮ ከልጁ ጋር ስላደገ ዝንቱ ዘመድ ይባላል /አብሮ አደግ አጋንንት እንደማለት ነው/ ሰውየውም ልጁ እንዲማርለት ወደ ሐዋርያቱ አምጥቶ ለመናቸው፤ እነሱም ገና እምነታቸው ለጋ ነበርና አጋንንቱ ሊወጣላቸው አልቻለም ነበር፤ ሰውየውም ወደ ጌታ አመጣው; የድንግል ማርያም ልጅ ገባሬ ተዓምር ኢየሱስ ክርስቶስም ያን ልጅ ፈወሰው; ሐዋርያቱም ለምን ለእኛ አቃተን አሉት; ጌታም ይህ አጋንንት ያለ "ፆምና ያለ ፀሎት" አይወጣም አላቸው!!! ማቴ 17:21። ፆም አጋንንትን ለማውጣን እንደሚጠቅም አስተማራቸው፤ ይህ ክፍል ስለጾም ስለሚናገር መናፍቃኑ "ቀላል አማርኛ" በሚሉት መፃህፋቸው የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 17 ቁጥር 21 ላይ ያለውን ቃል ዘለውታል; ቁጥሩ እንዳለ የለም፤ የእንግሊዘኛውን መፃህፍ ቅዱስ ስንመለከት ለምሳሌ Good news የሚለውን ብናይም ይህ ቁጥር የለውም!!

+++ የሐዋርያው ማቴዎስ ሰማዕትነት፦ ሐዋርያው ማቴዎስ በሃገራች አስተምሯል ብለናል፤ ብዙ ሐዋርያት ባስተማሩበት ሐገር ሰማዕትነትን መቀበል ግድ ሆኖባቸው ነበር; ሐዋርያው ማቴዎስ ግን በሃገራችን ሰማዕትነትን አልተቀበለም፤ ሃገራችን ልዩ የሚያደርጋትም ክርስትናን የተቀበለችው የአንድም ሐዋርያ ደም ሳታፈስ ይኩንኒ /ይሁልኝ/ ብላ በመቀበሏ ነው። ጤዛ ልሰው; ዳዋ ጥሰው; ዋዕይ ቁሩንም ታግሰው በየበረሃው የሚጸልዩ ፃድቃን አሉን፤ ሃገራችን ብትታረስ የሚበቅሉ ብዙ ቅዱሳን ጻድቃን አሏትና። ማቴዎስ ጥቅምት 12 ቀን ዐንገቱን ተሠይፎ ዐርፏል።

+++ አዋልድ መጽሐፋና ማቴዎስ፦ አዋልድ መጽሃፍ ማለት ከመጽሐፍ ቅዱስ ሐሳብ ያልወጡ ቅዱሳን መጽሐፍት ናቸው። መናፍቃኑ ከመፅሐፍ ቅዱስ ውጪ ምንም አይነት አዋልድ መጽሐፍትን አይቀበሉም። ለምን ሲባሉ ከዚህ መጽሐፍ አንዳች የሚጨምር ወይም የሚቀንስ ፍርድ ይጠብቀዋል የሚለውን የራዕየ ዩሐንስን የመጨረሻ ምዕረፍ ይጠቅሳሉ ራዕ ምዕ 22:18 ፤ እኛ ተሳስተናል ማለት ነው እንዴ? ካልተሳሳትን እንዴት እንዲህ ተብሎ ተጻፈ?

መናፍቃኑ መጽሐፍ ቅዱስን ቅንጭብ ቅንጭብ አድርገው ስለሚያነቡ ይስታሉ፤ ጌታም አስቀድሞ መፃህፍትን ስለማታውቁ ትስታላቹ እንዳለ፤ ወደ መልሱ እንመለስ; መናፍቃኑ መፅሐፍ ቅዱስን ልክ እንደ ስምንተኛ ክፍል የሳይንስ መጽሐፍ ያዩትና ዘፍጥረትን ምዕራፍ አንድ ራዕይን ደግሞ የመጨረሻ ምዕራፍ አድርገው ይቆጥሩታል፤ ይህ ግን የተሳሳተ ሐሳብ ነው። መፅሐፍ ቅዱስ የተጻፈው በአንድ ወቅትና በአንድ ሰው አይደለም; መጀመሪያም አንድ ጥራዝ አልነበረም ፤ ሐዋርያው ዩሐንስም በዚህ መጽሐፍ መጨመርም ሆነ መቀነስ እንደማይገባ የነገረን ለራዕዩ ነው እንጂ አዋልድ መፅሐፍትንማ ሐዋርያቱም በመፅሐፍ ቅዱስ ተጠቅመዋል እኮ!!! ልብ በል ከርዕሴ አልወጣሁም ከማቴዎስ ጋር እየተዋወቅን ነው፤ እስቲ ሐዋርያው ማቴዎስ ስለ አዋልድ መፅሐፍት ምን እንዳለ እንይ፦

+++ ለምሳሌ ማቴዎስ 2:23፦

“በነብያት ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈፀም ዘንድ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ ገብቶ ኖረ”

እስኪ መናፍቃን ይመልሱ; በነብይ ናዝራዊ ይባላል ተብሎ የተጻፈው ትንቢት በመፅሐፍ ቅዱስ የተፃፈው የቱ ጋር ነው? ከዘፍጥረት እስከ ራዕይ ብንፈልግ ይህን ትንቢት አናገኝም፤ ነገር ግን ሐዋርያው ማቴዎስ በወንጌሉ ፃፈው; ከየት አግኝቶ ጻፈው ቢሉ ይህ ትንቢት በነብያት ተነግሮ በምርኮ ግዜ በጠፉት መጻሕፍት የነበረ ሲሆን መጻሕፍቱ ቢጠፉም በቃል ለሐዋርያት ደርሷል፤ እናም ይህች ትንቢት በማቴዎስ ወንጌል ተጻፈች!!! ሐዋርያዊት የሆነችው ቤተክርስቲያናችን አዋልድ መጻሕፍትን የምትጠቀመው ሐዋርያቱ እነ ማቴዎስና ቅ/ጳውሎስ እንዳስተማሯት ነው ማለት ነው።
“በእግዚአብሔር መንፈስ የተፃፈ መጽሐፍ ሁሉ ለተግሣጽና ለትምህርት ይጠቅማል” 2ኛ ጢሞቴዎስ 3:16

የሐዋርያት ሥራ /acts of the apostles/ ወይም ግብረ ሐዋርያት ማለት ሐዋርያቱ የሰሩት ተጋድሎ ማለት አይደል እንዴ? እነ ሐዋርያው ያዕቆብ በሰይፍ ሲገደሉ በገድለ ሐዋርያት ተጽፏል የሐዋ. 12:1 ፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰማዕትነቱ የተጻፈለት ሐዋርያ ቅ/ያዕቆብ ብቻ ነው፤ ታዲያ የሌሎች ሐዋርያት ሰማዕትነትን መቀበል የለብንም ማለት ነው? መናፍቃኑ እንዲህ ካሰቡ “ሁለት ዓይን አለኝ ሁለቱም በደንብ ያያሉ ነገር ግን በአንዱ ዓይኔ ብቻ ነው ማየት የምፈልገው እንደማለት ይሆንባቸዋል!” ዩሐንስ በወንጌሉ እንዲህ አለ፦ “ጌታ ያደረገውን ተዓምራት ሁሉ ልጻፍ ቢሉ ለተዓምራቱ መጻፊያ አለም ባልበቃም ይመስለኛል” የዩሐ. 21:25 ፤ ጌታ ያደረጋቸው ተዓምራት ብዙ ናቸውና; በተዓምረ ኢየሱስ ላይም የተፃፈው ይህ እውነታ ነው። ጌታ ያደረገውን ተዓምር ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ አላምንም ማለት ደጎሞ “ሁለት ዓይን ነበረኝ አሁን ግን እንደ በጥለሚዎስ እውር ሆንኩኝ” ማለት ይሆናል ማለት ነው። በጥለሚዎስስ የዳዊት ልጅ ሆይ ማረኝ ብሎ የዓይን ብርሐኑን አግኝቷል። እኛንም ዓይነ ልቦናችንን ለቃሉ ያብራልን፤ አሜን

ወ ሥ በ ሐ ት ለ እ ግ ዚ አ ብ ሔ ር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር ፤ አሜን

ይህን የመሳሰለውን ማንበብ ቢፈልጉ ይህን ይመልከቱ
http://yonas-zekarias.blogspot.com/

12 comments:

Addis Gebyhu said...

Keber lemegabawe kiberen sete, khy yagelegelot zemanehen yebareke

Wondim Bekele said...

በቅዱሳን ላይ በትዕቢት የሚናገር አንደበት ዲዳ ይሁን!
[መዝሙረ ዳዊት 30:18]

Yeti Mehari said...

Kale hiwet yasemalen Egziabher yagelglot zemenhen yibarkleh . !!

Enzemir Ledingel Mariam said...

wow, le kidus temerteh dengil mariam atsefawen tekfelh......

Yemeskel Setota said...

kale hiwot yasemalen!! gerum temhert fetari yebarkeh

Alemeshet Gebremariam said...

Egziabhare yakbrelgne alchalkum eko kante wede ena share lmadreg andandu yaschgral Embete Tsegawen Tabzalh Wendema betam bezu nger Temrabetalhu bmtawetachewe tsehufoche Wendeem ehtochachenm byayut post ymtadergachwen ngroche bzuwoche ende ena limarubet yechelalu beya asebalhu Egziabhare Yebarkeh !!!!

Mekedese Negbashe said...

kale eywete yasemaleye ymefelegewene newe yageyewete

Wondim Bekele said...

Do you know what an interesting post you have! Am proud of you! Yekidusanochu bereket ayleye! Thank you!

Bili Mehari said...

Bante lay adro yastemaren EGZIABHER yemesgen balehbet tsegawn yabzaleh yekedusanochu bereket yederben behaymanotachen yatsnan!tebarek wendme.

your Sunday school brother. said...

By the name of God selam tenayestilign.
I read the attached PDF file it is nice and good .could you place do the same for future.
Melkam GENA

Bezuayehu Gugsa · Friends with Enat Tsega said...

kenemelaw betsebocheke melkam beal endhonelke emagalhu.

Bili Mehari said...

AMEN!!!melkam yeledet beal yehtnleh.wendme yonas!