Friday 28 December 2012

“የዘር በሽታ አይምታችሁ”


የእይዬ ጣይቱን ግጥም ልጋብዛችሁ

በሶማሊያ ችግር አብረን ስንጨነቅ
በዩጎዝላቪያ ቆመን ስንሳለቅ
በእንጀራ አባታችን በሩሲያ ስንስቅ
በእነሱ ሳንማር ካለፍን በዋዛ
አርባ መንግሥት ሆነን ክልል ስናበዛ
እንዳንጠያየቅ ፓስፖርትና ቪዛ!




ኢትዮጵያዊ መልኩን ነብር ዥንጉርጉርነቱን ይለውጣልን? “ ተብሎ በታላቁ መፅሐፍ ተጽፏል። ነብር እስከ ዛሬ ድረስ ዥንጉርጉርነቱን አልለወጠም፤ ኢትዮጵያዊያን ግን መልካችንን ከለወጥን ዘመናት አልፈዋል። ኢትዮጵያዊ መልኩን ነብር ዥንጉርጉርነቱን ይለውጣልን? ስንባል እኛ ደግሞ “የእናት ሆድ ዥንጉርጉር እንደ ነብር ጸጉር” ብለን ዘር በዘር ሆነናል! ደም ከደም ስር ጋር እንደማይጋጭ ሁሉ ኢትዮጵያዊነት ከዘር ጋር አይጋጭም ብንል ሞኞች ነን። አሁን ማን ይሙት ኢትዮጵያዊነቱ ከዘሩ ጋር ያልተምታታበት የት ይገኛል? እዚህ ጋር አንድ እውነተኛ ታሪክ ላውጋችሁ። አንድ ዘረኛ ሰው ነበር አሉ። እናላችሁ ይህ ዘረኛ ሰው ከእርሱ የባሰ ዘረኛ ሚስት አገኘና አገባት። ሲጀመር አንድ ዘረኛ ብቻ ነበር አሁን ግን ሁለት ጥንድ ዘረኛ ሆኑ። እናላችሁ ዘረኞቹ ወላጆች ልጃቸው ለአቅመ ዘረኛነት ሲደርስ አሪፍ ዘረኛ ሴት እንዲጠብስ አደረጉት። እንዲህ ያደገ ልጅ ደግሞ የሀገር ፍቅር ሳይሆን የዘር ፍቅር ይይዘዋል። እናማ አዲስ የተጣበሱት ዘረኞቹ ወላጆቻቸውን ለመምሰል ይሞክራሉ። የጎባጣ አሽከር ጎንበስ ብሎ ይሄዳል፤ ለምንድን ነው ሲሉት ጌታዬን ለመምሰል ነው አለ አሉ። ልጆቹም ወላጆቻቸውን ለመምሰል ዘረኛ ቢሆኑ አይደንቅም። የዘር ፍቅርን የሚያስተምር ወላጅ ሞልቷል፤ የሀገር ፍቅርን የሚያስተምር ወላጅ ማን ይሆን? ከእባብ እንቁላል ርግብ አይፈለፈልም አይደል የሚባለው።

የዘር በሽታ አይምታችሁ”  

ሕሊናን የሚያስደምም አንድ እውነተኛ ታሪክ ላውጋችሁ። በለንደን ከተማ የሚኖሩ ዘራቸው አንድ ግንድ የሆነ ሁለት ዘረኛሞች ነበሩ። ከሁለቱ አንደኛው አቡሽ የሚባል የልብ ጓደኛ ነበረው። እናላችሁ እነዚህ ሁለት የዘር ጓደኛሞች እንዲህ ሲሉ በአቡሼ ላይ ተማከሩ። ከሁለቱ የዘር ጓደኛሞች አንደኛው ለአቡሼ ጓደኛ እንዲህ አለው፦ አቡሽ የልብ ጓደኛህ ነው፤ ስለዚህ አቡሽ ቤቱን እንዲያከራየኝ አድርግና ለመንግስት እናጋልጠው፤ ከዚያም ቤቱ ተቀምቶ ለኛ ይሆናል ብሎ መከረው። የአቡሼ የልብ ጓደኛ ግን ነገሩ በጣም ከበደው። ሲያስበው ሲያሰላስለው ግን ከአቡሼ ጋ በዘር አይገናኙም። እየደጋገመ ሲያስበው የዘሩ ነገር ቆረቆረችውና ከጀርባ ሆድ ይቀርባል” ብሎ የልብ ጓደኛውን አቡሼን ከዳው። እባብ የሚገድለው በምላሱ ነው እንዲሉ በምላሱ የአቡሼን መቃብር ቆፈረለት። አቡሼ የስደትን ህይወት ለማሸነፍ የሚታገል ልጅ እግር ነገር ነበርና ትንሽ ሳንቲም ተቀብሎ ቤቱን አከራያቸው።

ከሁለት ወር በኋላ ሁለቱ የዘር ጓደኛሞች በእጃቸው ያለውን ማስረጃ ይዘው አቡሼን ለመንግሥት አጋለጡት። አቡሼ ነገሩን ሲሰማ ደንግጦ ብራቸውንም በሙሉ መልሶ ከቤቱ እንዲወጡለት ብዙ ለመናቸው። እነሱም ብራቸውን ተቀብለው እንደሚወጡ ነገሩት። በነጋታው ወደ ማታ አካባቢ አቡሼ ከስራ ወደ ቤቱ ሲመለስ የቤቱ ቁልፍ ተቀይሮ ጠበቀው። አቡሼ ክው ብሎ ቀረ። ስልክ ቢደውልላቸውም አላነሳ አሉት። ምስኪኑ አቡሼ ከእራሱ በተቀበሉት ብር ቁልፍ ገዝተው ቤቱን ከርችመውበት የጎዳና ተዳዳሪ እንዳደረጉት አወቀ።ሰውን ማመን ገደለኝ እኔን እየመሰለኝ” ብሎ አቡሼ ተማረረች። እውነትም በዘር እሱን ስላልመሰሉት ተረቱ ገጥሞለታል።

አሁን አቡሼ ያለው እድል ሁለት ብቻ ነው። ቤቱን በፈቃዱ መልቀቅ አልያም ፍርድ ቤት ሆሄዶ መከራከር። ፍርድ ቤት ለመከራከር ግን የአምስት መቶ ፓውንድ ጠበቃ ማቆም አለበት። በክርክሩ ቢሸነፍ ደግሞ መቶ ሺሕ ፓውንድ አካባቢ መክፈል አለበት። ምስኪኑ አቡሼ ይህንንም ያንንም ሲያወጣና ሲያወርድ አእምሮው ተነካ። አሁን ገና በራልኝ አለች እብድ ቤትዋን አቃጥላ” የሚለው ተረት በእኔ ሰራ እያለ እንደ ማበድ አደረገው። “እንኳን ቤትና የለኝም አጥር እደጅ አድራለሁ ዘረኛን ስረግም” የሚለውን የቴዲ አፍሮን ግጥም እያዜመ በየመንገዱ እየጮኸ መዞር ጀመረ። እናላችሁ እናቱ በስንት መከራ አባብላ እንዲረጋጋ አደረገችው። አቡሼም ቤት ቢወሰድ የዘጠኝ ወር ቤቴ እናቴ አለችልኝ ብሎ ተፅናና።

ይህ በቅርቡ በለንደን ከተማ የተፈፀመ እውነተኛ ታሪክ ነው። ሁለቱ ጓደኛሞች በአቡሼ ላይ የፈፀሙት የዘረኝነት ስራ በአጋጣሚ ነው ትላላችሁ? አጋጣሚ ነው የሚል ሊኖር ይችላል። እኔ ግን ሁሉም የራሱን ዘር እቅፍ ድግፍ ሲያደርግ ብዙ ሺሕ ጊዜ አይቻለሁ። አቡሼ ላይ የደረሰውም ይህ የዘረኝነት ክፉ በሽታ” ነው። እንደ ዘር በሽታ ክፉ የሆነ በሽታ ማንም የለም።


የዘር በሽታ አይምታችሁ”  

ኢትዮጵያ የተባለች እናት ብዙ ልጆች ወለደች አሉ። ይህች የተባረከች እናት ከ 80 በላይ ልጆችን በሰላም ተገላግላለች። ኢትዮጵያ ልጆችዋን በስማቸው ትጠራቸው ዘንድ ዳቦ ቆርሳ እንዲህ ብላ ስም አወጣችላቸው። ጋምቤላ ፣ ጉራጌ፣ ኦሮሞ፣ ወላይታ፣ትግሬ፣ጎጃሜ፣፣ አማራ ወዘተ ተብለው መጠራት ጀመሩ።

የኢትዮጵያ ልጆች ሲኖሩ ሲኖሩ አብረው እየተላፉ እየታገሉ እየተቃለዱ መኖራቸውን ረሱ። ውኃ ተራጭተው አፈር ፈጭተው መኖራቸውን ፣ በአንድ ትሪ እየተሻሙ መብላታቸውን ረሱና በቆራጣ ዐይን መተያየት ጀመሩ። እንደ ጉድ ተከፋፈሉ እንደ ጉድ ተናናቁ። ይህን ሁሉም በልቡ ያውቀዋል አሉ። ሁሉም በሩን ዘግቶ ስለራሱ ታላቅነት ማውራትም ጀመረ። ሁሉም ተሸፋፍኖ ይህንንም ያንንም ያማ ጀመር። ተሸፋፍነው ቢተኙ ገላልጦ የሚያይ አልላክ አለ ይባላል። በተለይ በስደት ያሉ የኢትዮጵያ ልጆች ልክ እንደ ነጮቹ ጥርሳቸውን ብልጭ እያደረጉ መፎጋገር ጀምረዋል አሉ። ይህን ጊዜ ነው ወላድዋ ኢትዮጵያ ክፉኛ ያዘነችው።


ከኢትዮጵያ ልጆች አንዱ ምን አለ መሰላችሁ? አሁን ደግሞ እኔ 20 ዓመት ብገዛ እንዴት አሪፍ ነበር ብሎ ምኞቱን ተንፍሷል። ያልሞተና ያልተኛ ብዙ ይሰማል አሉ! መቼስ የማይሰማ የለም ሁሉም እናቱን መግዛት ይመኛል ማለት ነው! እንግዲህ ሁሉም 20 ዓመት እናቱን መግዛት ከተመኘ 20 ዓመት x 80 ልጆች = 1600 ዓመት! ይህም ማለት እናት ኢትዮጵያ 1600 ዓመት በልጆችዋ ትገዛለች ማለት ነው። ድንገት ድጋሚ መግዛት እፈልጋለሁ የሚል ቢኖርስ…. ብቻ አያድርስ ነው።

ይሔ ሁሉ የዘር መብዛት ለምን አስፈለገ? እኔ የማምነው ሀገሬ ኢትዮጵያ ዘሬም ኢትዮጵያዊ መሆኔን ነው። ሌላው ለእኔ የዘር በሽታ ነው። በእርግጥ ይህ ብዙ የአስተሳሰብ ለውጥ ያስፈልገዋል። በአንድ ለሊትም አይሆንም። ኢትዮጵያ ግን ፩ድ እና ፩ ብቻ ናት። ይህ ማለት ባህሉ ስልጣኔው ይደምሰስ ይውደም ማለት አይደለም። ኢትዮጵያ ከሌለች ይህ ሁሉ ባህል እነዚህ ሁሉ ልጆች የሉም። ሁሉም ባህል ባይኖር ግን ኢትዮጵያ ትኖራለች። ይህም ያም ባህል “የኢትዮጵያ ባህል ይባላል ማለት ነው።

በተረፈ እኔ  የማምነው  ሀገሬ ኢትዮጵያ ዘሬም ኢትዮጵያዊ መሆኔን ነው!!

ልብ ብለን ስናስተውል እራሳችንን ካልፎገርን በስተቀር ዛሬ ዛሬ ሁላችንም በዘር በሽታ ተመትተናል። አንዲት ክብርት ኢትዮጵያ ሳትሆን በየልቡናችን ብዙ የዘር ሀገር አሉ። እንደ ዶሮ ብልት ለአስራ ሁለት መገነጣጠል የሚል ሐሳብም የሚመጣው በዘር በሽታ ስንመታ ነው። ይህ ደግሞ ያስፈራል። የተነቃነቀ ጥርስ ሳይወልቅ አይቀርም አሉ።


እኔ ብናገር አያምርም፤ ይሄ አህያ ታሟል አለ ጅብ! እስኪ እኔ ከምናገር እትዬ ጣይቱ ይናገሩ። እትዬ ጣይቱ የሚናገሩት አስደሳች አባባል አለ እኔ  የማምነው ሀገሬ ኢትዮጵያ ዘሬም ኢትዮጵያዊ መሆኔን ነው!!” የምትል አስደሳች አባባል አለቻቸው። እስኪ እኛም ይልመድብን። እስኪ ባለሥልጣኖችም ይልመድባችሁ። እስኪ ሁላችንም “እኔ  የማምነው ሀገሬ ኢትዮጵያ ዘሬም ኢትዮጵያዊ መሆኔን ነው!!” እንበል።


እትዬ ጣይቱ እንዲህ ብለው መመረቅ ይወዳሉ።


የዘር በሽታ አይምታችሁ”



Like ·  · 

No comments: