Friday 6 July 2012


ክርስትና እስልምና በኢትዮጲያ

አንድ የእስላም ባለ ሀብት ቤተክርስቲያን ለማሰራት ገንዘባቸውን ሰጡ አሉ። ቤተክርስቲያኑ ከተሰራ በኋላም በየአመቱ ኩንታል ጤፍ እየላኩ በዓላችሁን አክብሩበት ይሉ ነበር! እስላሙ ሕብረተሰብም በጉልበቱ ቤተክርስቲያን ሲሰራ ታይቷል። ክርስቲያኑም እንዲሁ ከእስላም የሃይማኖት መሪዎች ጋር በመሆን መስጊድ ሰርቷል። ይህ ነው ኢትዮጲያዊ ውበታችን!! ይህ ነው ከዓለም የሚለየን ውበታችን!!

ናይጄሪያ ነዳጅ ከማግኘትዋ በፊት ሰላም ነበረች። ነድጅ ስታገኝ የውጪ ኃይል ሰርገው ገቡና ከፋፈሏቸው። አይ ከዚያማ! እንደ ጉድ ተከፋፈሉ! እንደ ጉድ ተባሉ! እንደ ጉድ ተዘነጣጠሉ! እንደ ጉድ አለቁ! ይህን አታሳየኝ አለች ሴትዮዋ ይህንንስ ከኛ ያርቅልን። አንድነታችንና መቻቻላችን የሚፈተንበት ጊዜ አለ። የውጪ ኃይሎች ሰርገው ሲገቡ እንደ ጉድ እንፈተናለን እንደ ጉድ ብንከፋፈል እንደ ጉድ እናልቃለን ፣ እንደ ጉድ አንድ ብንሆን እንደ ጉድ እናድጋለን።

በፌስ ቡክ እና በ you tube ላይ የአክራሪነት መልእክት ያቀነቀኑ አሉ። እንጋደል፣ እናቃጥል፣ እንግደል የሚል ዜማ አውጥተው ነጠላ ዜማቸውን በቅርቡ የለቀቁ አሉ። ቢቻል ኦርጂናል ሲዲውን ካልሆነም ኮፒውን እንድንገዛ ብዙ አስተዋውቀዋል!  እውነተኛይቱ ሃይማኖት ግን እንዲህ አትልም። እውነተኞቹ የእስልምና አባቶች አክራሪነትን ስላልመረጡ ከስራቸው ተባረሩ። ለብዙ ዘመናት በየመስጊድ ጸሎት ሲያሰሙ የነበሩ ኢማም አክራሪ ስላልሆኑ ተባረዋል። እውነተኛቹ የእስልምና አባቶችና የእስላሙ ሕብረተሰብ የዋህ ናቸው። በአክራሪ ስም ቤተክርስቲያንን የሚያቃጥሉና ሰውን የሚገድሉ መጥፎ ፎቶዎችን በሕሊናችን ቀርጸዋል እንጂ የእስላሙ ሕብረተሰብ ማን እንደሆኑ የዋህ የሰላም ሰዎች እንደሆኑ በሚገባ እናውቃለን!

ቅ/ራጉኤል ቤተክርስቲያን ባሰራው ት/ቤት በምማርበት ጊዜ ከጎናችን መስጊድ አለ። ይህ መቻቻል ነው። በሌላው ዓለም ይህን እናድርግ ቢሉ ተባልተው ያልቃሉ እንጂ ይህ አንድነት የላቸውም። ባለሁባት በለንደን ከተማ የእስላም ሰፈር ለብቻው አለ። ክርስቲያኑ ደግሞ በተለየ ሰፈር ይኖራል። ይህ በሀገራችን ያለውን መቻቻል ፍንትው አድርጎ ያሳየናል።

 ሙሐጅር ለማ የሚባል ጓደኛ ነበረኝ። ከልጅነት ጀምሮ አብረን ነው ያደግነው። ትንሣኤ ሲሆን እኛ ቤት አይቀርም። እስላም እንደመሆኑ ለጓደኛዬ ብቻ ተብሎ የሚሰራ ምግብ አለ። የእስላም በዓል ሲሆን ደግሞ ቤታቸው እሄዳለሁ። እናትየው ለእኔ ብቻ ብለው የሰሩትን ምርጥ ምግብ እየደጋገምኩ እበላለሁ። ይህ ነው መቻቻል። ይህ ነው አንድነት። ይህ ነው የኢትዮጲያ ውበት። ክርስቲያኑ ሠርግ ቢደግስ ለእስላሙም ብሎ የተለየ ምግብ ያዘጋጃል። እስላሙም እንዲሁ። ልዩነታችን ውበታችን ነው! እዚህ ጋር እውነቷን መናገር አለብኝ። ስለ እስልምና እምነት ያለኝ አመለካከት የተዛባ ነበር። ለምን ቤተክርስቲያን ያቃጥላሉ፤ ለምን ሰው ይገድላሉ? ለምን? ምን ዓይነት ሃይማኖት ነው? የሚል የሕሊና ጥያቄ ነበረኝ። ይህ አመለካከቴ ግን በፍጹም ትልቅ ስህተት መሆኑ ገብቶኛል። ሃይማኖቱ ይህን አይልምና። እውነተኞቹ የእስልምና ሰዎች እምነታችን ይህ አይደለም እያሉ ኡ ኡ ብለው ሲጮሁ ዓይተናልና። ይህን ሁላችንም መረዳት ዓለብን። አክራሪ ነኝ የሚለ የኢትዮጲያ ጠላት ነውና በክርስቲያኑም ሆነ በእስላሙ ሕብረተሰብ መገለል አለበት።

ሁሉም ዜጋ እንዳይዘናጋ አለች ሴትዮዋ!


ከእስልምና ወደ ክርስትና የተቀየረ አንድ ሰው አውቃለሁ። ይህ ሰው መላ ዘመኑን  አክራሪ በሚባሉ ሰዎች እየተሰደደ ነው። የሃይማኖት ነጻነት የለም እንዴ? አንዱ እስላም ቢሆን እንዴት ብዬ መፎከር የለብኝም። የሰው ልጅ ክቡር ነውና ሃይማኖቴን እንደ ኮምፒዩተር ዳውንሎድ ላደርግበት አልችልም። ሲጀመር ፈጣሪ የሰጠውን ነጻነት የምነፍገው እኔ ማን ነኝ?  ፈጣሪ ከእውነተኛይቱ ሃይማኖት ውጪ ያሉትን ሰዎች ላጥፋ ቢል የእኛን እርዳታ አይፈልግምና!! ብዙ ሰዎች ያልተረዱት ይህንን ነው። ለሃይማኖት ተቆርቋሪ የሆኑ እየመሰላቸው ሃይማኖታቸውን ያስንቃሉ ያስገመግማሉም። ሃይማኖታቸው ስለ ፍቅር እያስተማራቸው እነሱ ግን ሕገ ወጥ ሕግ አስከባሪ ይሆናሉ!

  በየቤቱ ወረቀት እየተበተነ አክራሪ ሁን ማለቱንም የሃይማኖት አባቶች ተቃውመውታል። ይባስ ብሎ ከሃይማኖትህ ውጪ ጓደኛ አትያዝ ማለት የጀመሩም አልጠፉም። አንዳድ ጊዜ ደግሞ የፌስ ቡክ ጦርነትም አለ። በፌስ ቡክ የሚከራከሩ ሰዎች አይገርሟችሁም? አንዱ ይነሳና እኔ እምነቴ ክርስቲያን ነው ይልና ክርስቲያን ያላስተማረውን የሚተርክ አለ። ሌላውም እስላም ያላስተማረውን የሚተነትን አለ። አንዳንዶች ባለማስተዋልም ሆነ ሆን ብለው ሀገርን የሚያጠፋና የማይጠፋ እሳት  የሚያቀጣጥሉ አሉ። እነዚህ ሰዎች የኢትዮጲያና የሰላም ጠላቶች ናቸውና ሊገለሉ ይገባቸዋል። እነዚህ በሕሊና አናሳ የሆኑ ሰዎች ፍቅርን፣ ሰላምን፣ መቻቻልን፣ ሃይማኖትን ንቀዋልና ሊገለሉ ይገባቸዋል!!

ሰው ገድለህ ትድናለህ የሚል ሃይማኖት አልተፈጠረም። ይህን አይነቱ ሰው ሰይጣንም አብደሃል ሳይለው አይቀርም። ምክንያቱም ሰይጣን እንኳን እኔ የማምነውን ካላመንክ ብሎ ሰውን አልገደለምና!! ከሰይጣን እምነት የባሱ ናቸውና ሊገለሉ ይገባቸዋል!! በጎ ሕሊና ላለው ሰው ይህ እብደት እንጂ ጤንነት አይደለምና።

ሰላም ለኢትዮጲያ ይሁን!


No comments: